• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

መስከረም 16 ቀን የ2006 ዓ.ም. የመስቀል ደመራ በዓል

September 26, 2013

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትኖሩ፣ የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣ በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ በቅዱስ ደሙ ፈሳሽነት ከኀጢአት፣ ከሞተ ነፍስና ከሲኦል ግዞት ነፃ አድርጎ ያዳነን ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ በሰላም አደረሳችሁ!!

‹‹መስቀል ዓለም የዳነበት የእግዚአብሔር ኀይልና ጥበብ ነው፤››
(1ቆሮ.1÷18-24)

የተወደዳችሁና የተከበራችሁ በመላ ኢትዮጵያና በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን ሆይ፡-

እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማንያን፣ መስቀልን በታላቅ ድምቀት የምናከብርበት ዋናው ምክንያት፤ መስቀል ሰዎችን ለድኅነት፣ ዲያብሎስን ለሽንፈት ያበቃ የእግዚአብሔር ኀይልና ጥበብ በመሆኑ ነው፤ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን፣ ከሰው ልጅ ውድቀት ጀምሮ እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ድረስ በነበረው ዘመን፣ በኀጢአት ምክንያት ሞተ ሥጋና ሞተ ነፍስ በሰው ላይ የሰለጠኑበት፣ ዲያብሎስ ኀጢአትን መሣርያ አድርጎ፣ በሞት አቀባይነት፣ ሰውን በሲኦል ውስጥ አጉሮ ያሠቃየበት ዘመን ነበረ፤ ሰው ለዚህ ዐይነቱ መከራ የተዳረገበት ምክንያት፣ የፈጣሪውን ትእዛዝ ተላልፎ በሠራው ኀጢአት በደለኛ ሆኖ በመገኘቱ ነው፤ በዚህም ተግባሩ እግዚአብሔር ተለየው፤ እግዚአብሔር ሰውን ሲለየው፣ ለሠራው ኀጢአት ቅጣት የሚሆን የሞት ፍርድም ፈርዶ ነው፤ ስለሆነም ሰው የተፈረደበት ጥፋተኛ በመሆኑ፣ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት አልነበረውም፤ ጠባቂ የሌላቸው በጎች፣ ለተኲላ ንጥቂያ የተጋለጡ እንደሚሆኑ ሁሉ፣ ሰውም እግዚአብሔር ሲለየው፣ ለዲያብሎስ የመከራ ግዛት የተጋለጠ ሆነ፤ ከአዳም ውድቀት እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ባሉት ዘመናት፣ ሰው ሁሉ በፍዳ ኀጢአት እየተሰቃየ በዲያብሎስ ከተማ በሲኦል ውስጥ ግዞተኛ ሆኖ ቁም ስቅሉን አየ፤ (1ጴጥ. 3÷18-19 )

ይሁንና እግዚአብሔር ሰውን ካጋጠመው መከራ አንድ ቀን እንደሚገላግለው በነቢያት አድሮ ትንቢት ሲያናግር፣ ምሳሌ ሲያስመስል፣ ሱባዔ ሲያስቈጥር ቆይቶ ዘመኑ በደረሰ ጊዜ፣ በሰው ላይ የተላለፈውን ፍርድ ወደ ራሱ አዙሮ፣ ሕጉ የጣለውን የሞት ቅጣት እሱ ራሱ ለመቀበል፤በመስቀል ላይ ተሰቅሎ መሥዋዕት ሆነ፤ በመሥዋዕትነቱም ሰውን ከፍዳ ኀጢአትና ከሞተ ነፍስ ነፃ አወጣው፤ ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ እንደጻፈው፡- በፊት የተሠራውን ኀጢአት ለመተውና በእርሱ የሚያምኑትንም በኋላ ከሚመጣው ኀጢአት ለማዳን እግዚአብሔር፣ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ማመንን የኀጢአት ማስተሥረያ አድርጎ አቆመው፤ ብሎአል፡፡ (ሮሜ 3÷25-26)

ጌታችን በዚህ በመስቀሉ ላይ በፈጸመው መሥዋዕትነት ምክንያት፣ ያለፈው ኀጢአትም ሆነ የኋላው ኀጢአት የሚደመሰስበት ሁኔታ ተፈጠረ፤ ከዚህ በኋላ ኀጢአትም፣ ሞትም፣ ዲያብሎስም ተሸንፈው ባዶአቸውን ቀሩ፤ ለሰው ከእግዚአብሔር መለየትና መቀጣት ዋና መንሥኤው ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ ነው፤ አለመታዘዝ የኀጢአት ምንጭ ሆነ፤ ኀጢአትም ሰውን ለፍርድ አጋለጠ፣ ፍርድም ለሞት የኀይል ምንጭ ሆነ፤ ሞትም በበኩሉ ለዲያብሎስ ከተማ ለሲኦል በኀጢአተኞች መሞላት ዋና ምክንያት ሆነ፤ አሁን ግን ክርስቶስ ለኀጢአተኞች ቤዛ ሆኖ በሰዎች ፈንታ በመስቀል ላይ በመሠዋቱ፣ የሰውን የኀጢአት ዕዳ ራሱ ከፈለና ሰውን ከኀጢአት ዕዳ ነፃ አደረገው፤ በዚህም የኀጢአትና የሞት ግንኙነት ተቋረጠ፤ ዲያብሎስም ከሰረ፤ ምክንያቱም በክርስቶስ ሞት ኀጢአት ተደመሰሰ፤ ኀጢአት ሲደመሰስ፣ ሰውም ከፍርድ ነፃ ሆነ፤ ሞት ይዞ የሚያቀርበውን ሲያጣ፤ ሲኦል የሚውጠውን አጣ፣ ዲያብሎስም ከሰረ፤ ማለትም ድል ሆነ፤ ተሸነፈ፤ መስቀል ያስገኘልን ድል ይህንን ነው፤ ለዚህም ነው መስቀል ሞዐ፤ ሞት ተሞአ፤ ወዲያብሎስ ወድቀ፤ መስቀል ድል አደረገ፤ ሞት ድል ሆነ፤ ዲያብሎስም ወደቀ፤ ብለው ቅዱሳት መጻሕፍት የምሥራቹን የሚነግሩን፤ (1ቆሮ.15÷54-57፤ ኤፌ.2÷16፤ ተሰ. 2÷14-15) እግዚአብሔር በዚህ ምክንያት ሰውን ታረቀው፤ ሰው ቀድሞ ከውድቀቱ በፊት የነበረውን ጸጋና ክብር ተመልሶለት ከእርሱ ጋር ኅብረት እንዲኖረው ፈቀደ፤ ኅብረቱም በእምነት፣ በጥምቀትና በቅዱስ ቊርባን ምሥጢር እንዲፈጸም አደረገ፤ ኀጢአት በዚህ ሲወገድ ሀብተ ጸጋ መጣ፣ ሀብተ ጸጋ ሲመጣ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ተመሠረተ፣ ሞተ ነፍስ ተሻረ፣ የሲኦል በር ተሰባበረ፣ ዲያብሎስም ባዶውን ቀረ፤ ሰው ግን ዘለዓለማዊ ሕይወትና ክብርን ተቀዳጀ፤ ስለሆነም በመስቀሉ ላይ በተፈጸመው የመሥዋዕትነት ኀይል በኀጢአታችን ከሚመጣብን ሞተ ነፍስና ከኵነኔ ሲኦል ድነናል፤ መስቀል የእግዚአብሔር ኀይልና ጥበብ ነው ብለን የምናምነውም በዚህ ኀይልና ጥበብ በመዳናችን ነው፤ መስቀልን ስናከብር በዋነኛነት የምናስበው፣ ክርስቶስንና የእርሱ የደም መሥዋዕትነትን ነው፤ ታላቁ ምሥጢርና የመዳኛችን አስኳልም ያለው በእርሱ ደም ውስጥ ነው፤ ይሁንና ደሙ የፈሰሰበት ትእምርተ መስቀልም ትልቅ ክብር ያለው ነው፤

ከኢትዮጵያ ሰንደቅ ዐላማ በስተጀርባ ያለው ትልቅ መልእክት የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነትና ሉዓላዊነት ነው፤ ሆኖም የኢትዮጵያውያንን ነፃነትና ሉዓላዊነት በውክልና የተሸከመው ሰንደቅ ዐላማም ልዩ ክብር አለው፤ እንደዚሁም ሁሉ በክርስቶስ ደም የተገኘው ዕርቅና ድኅነት በስተጀርባው ያዘለና የዳንንበት ደሙም የፈሰሰው በእርሱ ላይ መሆኑን የሚያስታውሰንና የሚያሳስበን ትእምርተ መስቀልም ከፍ ያለ ክብር የሚገባው በመሆኑ እናከብረዋለን፤ መስቀል በክርስትና ሃይማኖት ጠላቶች ተቀብሮ ደብዛው እንዲጠፋ የተደረገው ሤራ እንዲከሽፍ የሆነበትም ዋና ምክንያት፣ መስቀል በዓለም ላይ የክርስቶስን መሥዋዕትነትና አዳኝነት እንዲመሰክርና እንዲያሳስብ ተፈልጎ ነው፤ ስለዚህ ትእምርተ መስቀሉን ባየን ቊጥር የክርሰቶስን መሥዋዕትነትና ድኅነታችንን እናስባለን፤ እናስታውሳለንም፡፡

ስናስበውም ቀላል በሆነ ነገር ሳይሆን፣ ለታላቅ የአዳኝነት ምሥጢሩ በሚገባ፣ በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዐትና በታላቅ ድምቀት መሆን ይገባዋል፣ መስቀል በክርስትና ሃይማኖት ጠላቶች ከተቀበረ በኋላ፣ በንግሥት ዕሌኒ መንፈሳዊ ጥረት ከተቀበረበት ጒድጓድ የወጣበትን ታሪክ ለማስታወስ፣ እኛ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በየዓመቱ መስከረም 17 ቀን ከፍ ባለ ሥነ ሥርዐትና በታላቅ ድምቀት እናከብረዋለን፤ እግዚአብሔር በመጀመሪያ ሰውን ከረቀቀ ጭንቅላት ጋር ፈጠረው፤ ሰውም ከእግዚአብሔር በተሰጠው አእምሮ እየተመራመረና እየተራቀቀ አሁን በዐይናችን የምናያቸውን የጥበብ ውጤቶች ሠራ፤ ከዚህ አኳያ ሰውን ለመርዳት የሚያገለግል መልካም የጥበብ ሥራ ሁሉ የእግዚአብሔር ጥበብ ነው ብሎ መቀበል እውነት እንጂ ስሕተት አይሆንም፤ ዓለም በየጊዜው የሚያጋጥሙአትን ችግሮች ከእግዚአብሔር በተገኘ ጥበብ መከላከል ኀጢአት አይደለም፡፡

ከዚህ አንጻር በአሁኑ ጊዜ እግዚአብሔር ለሰዎች በሰጠው የሕክምና ጥበብ በዓለም አስከፊ የሆነውን የኤች አይ ቪ ቫይረስን መቀነስ የሚያስችል የዕድሜ ማራዘሚያ መድኀኒት መገኘቱ መልካም ነው፤ በሌላ በኩል ደግሞ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖቻችን ፈጣሪን በማመንና በመማፀን፣ እግዚአብሔር የመፈወስ ኀይልን ባሳደረበት በቅዱስ ጸበል እየተጠቀሙ ፈውስ ማግኘቱ የእግዚአብሔር የምሕረት ስጦታ ነው፤ ስለሆነም ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖቻችን፣ መድኀኒቱና ጸበሉ ሰውን ለማዳን ከእግዚአብሔር የተሰጡ መሆናቸውን አምነው ሁለቱንም በመውሰድ በሽታውን ቢከላከሉ ኀጢአት አይሆንባቸውም፡፡

ከዚህም ጋር የእናቶችን ሞትና ሥቃይ ለመቀነስ ታስቦ በሀገራችን እየተካሄደ ያለውን እናቶችን በእርግዝና እና በወሊድ ጊዜ የመርዳት ሕክምና፣ እግዚአብሔር እናቶችን ለማዳን ብሎ የገለጸው ጥበብ እንደሆነ መገንዘቡ ብልህነት ነው፡፡ በተለይም በነፍስ አባትነት የጥበቃ ሥራ የተሠማሩ ቀሳውስትና መምህራን፣ እንዲሁም ሰባክያነ ወንጌል፣ ሕዝቡን በሚያስተምሩበት ጊዜ፣ እናቶች የተለመደው የሃይማኖታችን እምነትና ጸበል እየጠጡና እየተቀቡ፣ እንዲሁም የሚወዷትን እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እየተማጸኑ፣ በሕክምና እየተረዱ ቢወልዱ በእግዚአብሔር የተወደደና የተፈቀደ ቅዱስ ተግባር መሆኑን በማስተማርና በማስረዳት፣ እናቶችን በወሊድ ከመሞት የመቀነስ መርሐ ግብሩ እንዲሳካ በሰፊው እንዲሠሩ ያስፈልጋል፡፡

የእግዚአብሔር ዐላማ ምን ጊዜውም ሰውን በሁለመናው ማዳን እንደሆነ እናውቃለን፤ በመሆኑም የእርሱ መልእክተኞች የሆን ሁላችን ሰው የሚድንበትን ሁሉ የማስተማርና የማስረዳት ግዴታና ኀላፊነት እንዳለብን መዘንጋት የለብንም፤ የመስቀል ምሥጢርም መዳንና ማዳን ነውና፣ አሁንም የማዳን ሥራውን ያለመታከት ማስተማር አለብን፤ ማስተዋልና ትጋት፣ ፍቅርና ስምምነት፣ መከባበርና መረዳዳት፣ መቻቻልና መተማመን ምንጊዜም መሣሪያዎቻችን እናድርጋቸው፤ ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን ሃይማኖትና ቋንቋ፤ ብሔርና ባህል ሳይለያያቸውና ሳይነጣጥላቸው፤ ለዚህ ዓይነቱ ስሜትም ሳይበገሩ፣ ሁሉም እንደ መስቀል ችቦ አንድ ሆነው የዚህችን ሀገር አንድነትና ነፃነት፣ ታሪክና ሉዓላዊነት ጠብቀው ያስረከቡን በፍቅር፣ በስምምነትና በአንድነት መሥዋዕትነትን እየከፈሉና በኅብረት እየሠሩ ነው፤ ስለሆነም ከጥንት ጀምሮ ተጠብቆ የቆየውን የሕዝባችን አንድነት፣ በሃይማኖት የመቻቻልና የመከባበር፣ ተስማምቶና ተጋግዞ በፍቅር የመኖር ልዩ ጸጋችን፣ ከሀገራችን አልፎ ለዓለም ሁሉ መልካም አርኣያ እንዲሆን፣ እንደዚሁም በመላ ሀገራችን ተቀጣጥሎ የሚገኘው ልማታችንን ከሚፈለገው ግብ ለማድረስ ዋናውና መሠረታዊ ግብአት ሆኖ የሚያገለግለን ስለሆነ፣ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን እንደ ዐይን ብሌን ልንጠብቀው ይገባል፡፡ ይህ የሆነ እንደሆነ ሀገራችን ከድህነትና ከጒስቊልና ተላቃ ከበለጸጉ የዓለማችን ሀገሮች እኩል የምትሰለፍበት ጊዜ እንዲመጣ በጒጉት እንጠብቃለን በብርቱም እንጸልያለን፡፡ ይህ እንዲሆንም ጠንክረን እንሥራ፤ በማለት ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት መልእክታችንን አደራ ጭምር እናስተላልፋለን ፡፡ መልካም የመስቀል በዓል ያድርግልን ፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ፡፡አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc2013-09-26 10:22:052024-12-05 10:24:07መስከረም 16 ቀን የ2006 ዓ.ም. የመስቀል ደመራ በዓል
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: የ2006 ዓ.ም ዘመን መለወጫ በዓል መስከረም 1 ቀን 2006 ዓ.ም Link to: የ2006 ዓ.ም ዘመን መለወጫ በዓል መስከረም 1 ቀን 2006 ዓ.ም የ2006 ዓ.ም ዘመን መለወጫ በዓል መስከረም 1 ቀን 2006... Link to: 32ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ ዓመታዊ ጉባኤ ከጥቅምት 4 እስከ 11 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to: 32ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ ዓመታዊ ጉባኤ ከጥቅምት 4 እስከ 11 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ 32ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ ዓመታዊ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top