መስከረም 1 ቀን 2010 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

የዘመናትና የፍጥረታት ፈጣሪ የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ማቴዎስ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት ወደ ዘመነ ማርቆስ ሁለት ሺሕ ዐሥር ዓመተ ምሕረት በሰላም አደረሳችሁ፡፡

“አንሶስዉ እንዘ ብክሙ ብርሃን
ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ።”
(ዮሐ. 12፥35)

የብርሃን ጸጋ ለሰው ልጆች ወይም በአጠቃላይ ለፍጥረታት ሁሉ ከተሰጡ የእግዚአብሔር ስጦታዎች ትልቁ ነው፤ ብርሃን የሥራ መሣሪያ ነው፣ ብርሃን የመልካም ነገር ሁሉ ተምሳሌት ነው፤ እግዚአብሔር ራሱ በባሕርዩ ብርሃን ከመሆኑም ሌላ በእርሱ ዘንድ የማይጠፋ ብርሃን እንዳለ በቅዱስ መጽሐፍ ተገልጾአል፤ የሰው ልጅ ከወዲያ ወዲህ፣ ከወዲህ ወዲያ ተንቀሳቅሶ፣ ነግዶ፣ አርሶ፣ ሠርቶ፣ ተምሮና አስተምሮ ለኑሮው የሚያስፈልገውን ሁሉ ለማግኘት ብርሃን የግድ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም ጋር ሙሉ ጤና፣ ቀና የሆነ አእምሮ፣ ሰላምና ፍቅር ለሰው ልጅ ብልጽግና ወሳኝ ቦታ አላቸው፤ እነዚህ በሰው ልጅ መንፈሳዊና ሥጋዊ ሕይወት ላይ ያላቸው ጸጋ እጅግ የላቀ በመሆኑ በቅዱስ መጽሐፍ አገላለጽ ብርሃን እየተባሉ ይጠቀሳሉ፡፡ እንደዚሁም ዕድሜና መልካም ዘመን በተመሳሳይ አገላለጽ ብርሃን ተብሎ ይመሠጠራል፤ ምክንያቱም ብርሃን በሌለበት ሁኔታ ምንም ሥራ መሥራት እንደማይቻል ሰላማዊ ዘመን ከሌለም ልማትና እድገት ማስመዝገብ አይቻልምና ነው፤ በመሆኑም ዕድሜና ዘመንም ሌላው ታላቁ የእግዚአብሔር ብርሃን ነው፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” ሲል የዕድሜና የጊዜ ብርሃንነትን ማመልከቱ እንደሆነ ዐውደ ምንባቡ በግልጽ ያሳያል፤ ምክንያቱም እርሱ በዚህ ዓለም በመምህርነት የተገለጸበት ዘመን ወደ መጠናቀቁ እየተቃረበ በነበረበት ጊዜ የተናገረው ከመሆኑ ጋር ባላችው አጭር የትምህርት ዕድሜ ወይም ዘመን ሰዎች በእርሱ ብርሃንነት እንዲያምኑ የቀሰቀሰበትና ያስተማረበት ትምህርት ነው፡፡ በእርግጥም ላስተዋለውና በሥራ ለተጠቀመበት፣ ጊዜ ታላቁ ብርሃን ነው፤ ጊዜ ሲቀና ነገሩ ሁሉ ብርሃን ይሆናል፤ ጊዜው ከጨለመ ደግሞ ዙሪያው ሁሉ ጨለማ ይሆናል፤ ዕድሜያችን ወይም ዘመናችን በሕይወታችን ውስጥ ለልማትም ሆነ ለጥፋት ለጽድቅም ሆነ ለኀጢአት፣ ለትንሣኤም ሆነ ለውድቀት መሣሪያነቱ የታወቀ ነው፤ ምክንያቱም ሁሉም የሚሠራውና የሚከናወነው በጊዜው ነውና፡፡ በዘመናት ውስጥ ብርሃናውያን የሆኑ ዓመታት እንደነበሩ ሁሉ ጽልመታውያን የሆኑ ዓመታትም በሀገራችንም ሆነ በሌላው ዓለም እንደነበሩ እናውቃለን፡፡ እነዚህ ተቃራኒ የሆኑ ነገሮች በየፊናቸው ለሰው ልጆች ያተረፉት ስጦታም በስማቸው ልክ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ዘመናትን ብርሃናውያን ወይም ጽልመታውያን እንዲሆኑ በማድረግ ረገድ የሰው ልጅ ሚና ትልቅ እንደሆነ የማይካድ ነው፡፡

የሰው ልጅ የማስተዋልና የመቻቻል፣ የመታገሥና የመወያየት፣ የፍቅርና የስምምነት፣ የሰላምና የአንድነት ጠቃሚነትን ዘንግቶ፣ በስሜትና በወቅታዊ ትኲሳት፣ እንደዚሁም የእግዚአብሔርን የሰላም ድምፅ አልሰማ ብሎ በራስ ወዳድነትና በስግብግብነት ተሸንፎ ወደ ትርምስ ሲገባ ዘመኑ ጽልመታዊ መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡ በሰው ችኩልና ደካማ አስተሳሰብ የተጨናነቀ ጽልመታዊ ዘመን ከውድመትና ከጥፋት በቀር አንዳችም ትርፍ እንደሌለው ከሀገራችን ተሞክሮ የበለጠ መምህር አይኖርም፡፡ በሌላ በኩል ሰዎች ከእርስ በርስ ግጭት ተላቅቀው ሰላምንና ፍቅርን፣ አንድነትንና እኩልነትን፣ መቻቻልንና መስማማትን፣ መወያየትንና መቀራረብን፣ ወንድማማችነትንና መከባበርን ያረጋገጠ፣ ትዕግሥትና አስተዋይነት የማይለየው የእግዚአብሔርን ድምፅ በመከተልና አእምሮን በማስፋት መኖር ሲጀመሩ ዘመኑ ብርሃናዊ እንደሚሆን፣ ልማቱና እድገቱም እንደሚፈጥንና እንደሚረጋገጥ አሁንም በሀገራችን ወቅታዊ ተሞክሮ ተረድተነዋል፤ ይህ ሁሉ እውነታ የሚያሳየው የዘመን ብርሃንነትና ጽልመትነት የሚወሰነው፣ እኛ ሰዎች በምናውጠነጥነው አስተሳሰብና በምናደርገው እንቅስቃሴ እንደሆነ ማስተዋል ተገቢ ነው፤ ለዚህም ነው ኀላፊነቱም ተመልሶ ወደ እኛ የሚመጣው፡፡

ጌታችንም ምርጫውንና ውሳኔውን ለእኛ ትቶ ብርሃን ስላላችሁ በብርሃን ተመላለሱ በማለት ገለጻውንና ትምህርቱን ብቻ መናገሩ ከዚህ የተነሣ እንደሆነ ማስተዋል ይገባል፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ የሚሻለንን መምረጥና መከተል የእኛ ፈንታ ነው፤ ምርጫችን ሰላምና አንድነት ከሆነ ዘመኑ ብርሃን ነው፤ ተቃራኒው ከሆነ ደግሞ የኋልዮሽ ጒዞ ይሆናል፤ ስለሆነም ምርጫችን ሰላምና አንድነት እንዲሆን ሁላችንም ተስማምተን መወሰን አለብን፡፡ ማንም ሰው ብርሃንና ጨለማ ጎን ለጎን ቀርበውለት የትኛውን ትመርጣለህ የሚል ጥያቄ ቢቀርብለት ያለማመንታት ብርሃኑን እንደሚመርጥ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ችግሩ ሰዎች ይህንን ግልጽና ጠቃሚ ምርጫ ተቀብለው ተጠቃሚ እንዳይሆኑ ብዙ የሚያታልሉና በድብብቆሽ የሚመላለሱ አካላት በመካከሉ ይገቡና ጨለማውን ብርሃን፣ ብርሃኑንም ጨለማ አስመስለው ሰውን ወደገደል መክተታቸው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ብርሃናዊና መልካም የሆነ ምርጫችንን ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ያደርጉታል፤ እኛ ሰዎች አእምሮአችንን በሚገባ መጠቀም ያለብን እዚህ ላይ ነው፤ ማለትም እኛው ራሳችን የሚጠቅመንና የማይጠቅመንን የመለየት ዐቅም ስላለን ዓቅማችንን ተጠቅመን ለዘላቂ ጥቅማችንና ለትክክለኛ ምርጫችን መወገን ይኖርብናል ማለት ነው፡፡

ሰዎች የሆን ሁላችን ባለ አእምሮዎች ሆነን ተፈጥረናል፤ አእምሮ ከእግዚብሔር ጋር የሚያመሳስለን ስለሆነ ከሀብት ሁሉ የበለጠ ሀብት ነው፤ ይህንን አእምሮአችንን ካዳመጥነውና ከተከተልነው ሐቁን አይስትም፤ አመዛዝኖ፣ ገምግሞ ለክቶ፣ ጠቃሚውን ነገር ከልባችን ውስጥ ቊጭ ያደርግልናል፤ ነገር ግን ትዕግሥትን፣ ማገናዘብን፣ ቆም ብሎ ማሰላሰልን፣ ምክንያታዊ መሆንን፣ ማመዛዘንን፣ ፈሪሀ እግዚአብሔርና ፈቃደ እግዚአብሔር መከተልን ይፈልጋልና እነዚህን እንደ ግብአት አድርገን ልናቀርብለት ይገባል፤ ይህንን መጠቀም ስንችል የዘመናችንና የዕድሜያችን ብርሃን ዋስትና ይኖረዋል፤ ጨለማም አያሸንፈውም፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

ለዐሥር ዓመታት ያህል የተጓዝንበት የሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዐቢይ ዘመን ለኢትየጵያ ሀገራችን ብርሃናዊ ዘመን የፈነጠቀበት ወቅት ነው፤ ምክንያቱም በዚህ ዘመን ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያልተነካ ሀብታችን እርሱም የዐባይ ወንዝ ሀብታችንን ለመቋደስ የሚያስችል ግዙፍ የልማት ሥራ ተጀምሮ ወደ መጠናቀቅ እየተቃረበ ያለበት እጅግ ብርሃናዊ ዘመን በመሆኑ ነው፡፡ በሠለጠነው የምዕራቡ ዓለም ካልሆነ በቀር በአፍሪከ ምድር ለዚያውም በድርቅ፣ በረኃብና በጦርነት ትታወቅ በነበረችው ኢትዮጵያ ይሆናሉ ተብለው የማይታሰቡ እጅግ ግዙፍ የሆኑና የሕዝባችንን መሠረታዊ የእድገት ለውጥ የሚያረጋግጡ የኮንስትራክሽንና የኢንዱስትሪ፣ የትምህርትና የጤና ተቅዋማት በፍጥነት እየገሠገሡ መገኘት በዚህ ብርሃናዊ ዘመን የዕለት ተዕለት ትእይንት እንደሆኑ በዐይን እየታየ ነው፤ ይህ ጸጋ እንዲሁ ያለ መሥዋዕትነት የተገኘ ሳይሆን እኛ ኢትዮጵያውያን ከሁሉ በላይ ሰላምንና ልማትን መርጠን በአንድነት ወደ ብርሃናዊ አስተሳሰብ ስለገባን ነው፡፡ እግዚአብሔርም በብርሃን ተመላለሱ ያለው ይህንን ለማመልከት ነውና በዚህ ምክንያት ትክክለኛ ምርጫችንን እርሱ ስለባረከልን የልማትና የእድገት ተምሳሌት መሆን እንደቻልን አንሥተውም፡፡ ዛሬም ወደማንወደውና ወደማንመርጠው ጨለማ ሊከቱን የሚሹ እንደ ኤች አይ ቪ ኤድስና ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር እንደዚሁም በሕዝባችን መካከል መለያየትና መቃቃር ሊያስከትሉ የሚችሉ አፍራሽ ድርጊቶች ብቅ ብቅ በማለት እየተፈታተኑን እንደሆኑ መዘንጋት የለበትም፤ እነዚህ ሁሉ በተግባር ያየናቸው የሕዝባችን ቀንደኛ ፀርና የጨለማ አበጋዞች፣ የልማታችንና የሰላማችን ዕንቅፋቶች ናቸውና ሕዝቡ በተለመደው ሃይማኖታዊና አርቆ ማሰብ ኀይሉ እንዲመክታቸው በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

በመጨረሻም፡ የዛሬ ዐሥር ዓመት “ታላቅ ነበርን ታላቅም እንሆናለን” በማለት ለሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዐቢይ ክፍለ ዘመን የገባነውን ቃል በማደስ በአዲሱ ዓመት ካለፈው ዓመት በበለጠ ጠንክረን በመሥራት ልማታችንንና እድገታችንን በፍጥነት በማሳደግ፣ የኤች አይ ቪ ኤድስ በሽታን ባለን የተሞክሮ አሠራር በመመከት፣ እንደዚሁም ሕገ ወጥ ዝውውርን፣ ሀገርንና ሕዝብን የሚጎዳ ድርጊትን በማክሸፍ፣ በሃይማኖትና በሰላም መርሕ በመመራት አዲሱን ዘመን ብርሃናዊ እንድናደርገው አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

አዲሱ ዘመን የሰላም የፍቅርና የብልጽግና ያድርግልን፤ እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡