ግንቦት 05 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

በየተሰማራንበት ሁሉ እግዚአብሔር እየረዳን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና የምግብና ሥራችንን እየተወጣን ከቆየንበት ሀገረ ሰብከት በሰላም አምጥቶና አንድ ላይ አሰባስቦ ስለ ሃይማኖታችንና ስለሀገራችን ለመወያየት የሰበሰበን እግዚአብሔር አምላካችን ስሙ የተመሰገነ ይሁን፡፡

“ትግሁ ወጸልዩ ከመ ኢትባኡ ውስተ መንሱት፤ ወደፈተና እንዳትገቡ ተግታችሁ ጸልዩ” (ማቴ-6፡1)፡፡ ፈጣሬ ፍጥረታት እግዚአብሔር ሕዝቡን የሚወድ ብቻ ሳይሆን ከሕዝቡ መለየት የማይፈልግ አምላክ ነው፣ የእግዚአብሔር መኖሪያ በሰው እጅ በተሠራው ቍሳዊ ነገር ሳይሆን እሱ ራሱ በሠራው በሰው ልቡና ስለሆነ፣ ከሰው ጋር መገናኘት የሚፈልገውም በዋናነት በዚሁ ስፍራ እንደሆነ እሱ ራሱ ነግሮናል፤ ታዲያ እግዚአብሔር ከሰው ልቡና መለየት እንደማይፈልግ ሁሉ ሰውም ምንም ደካማ ቢሆንም ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር መለየት አይፈልግም፤ ይህም የጋራ ፍላጎት ሊከናወን የሚችለው በእምነትና በጸሎት ነው፡፡ ይህ ግንኙነት የደጋፊና ተደጋፊ ዐላማ ያለው ግንኙነት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችንን በዚህ መልኩ በጸሎት ስንቀርብ በቀላሉ እንደምናገኘው እናምናለን፤

“ወሀቦ ለልዑል ጸሎተከ ትጼውዐኒ በዕለተ ምንዳቤከ አድኅነከ ወተአኵተኒ — ጸሎትህን ለልዑል እግዚአብሔር አቅርብ፤ በመከራህ ቀን ትጠራኛለህ፤ እኔም አድንሃለሁ፤ አንተም ታመሰግነኛለህ” ሲል ቃል ገብቶልናል፡፡ ይህ ወቅት በመላ ክፍለ ዓለም ተሰራጭቶ የሚገኘው የኮረና ቫይረስ በሽታ ፍጥረተ ሰብእን በጠቅላላ ከባድ ሥጋት ላይ የጣለበት ወቅት ነው፤ “በእንቅርት ላይ—-” እንደሚባለው ሀገራችን በሌሎች ውስብስብ ነገሮች በተወጠረችበት ወቅት ይህ ዐይነቱ መድኀኒት የለሽ በሽታ መከሠቱ በሀገራችን ላይ ሥጋት እንዲበዛ አድርጓል፡፡

ይህ ወቅት ለሀገራችንም ለቤተ ክርስቲያናችንም ለሕዝባችንም ከባድ የፈተና ወቅት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ እንደ ትናንቱ የመሰለ አካሄድና አስተሳሰብ ጭራሽ የሚያስኬድ አይሆንም፤ እኛ ሊቃነ ጳጳሳት የሕዝበ እግዚአብሔር እረኞች ሆነን እዚህ ላይ የተሰበሰብነው ሕዝቡን በሁለንተናዊ ሕይወቱ ከፈተና ለመጠበቅ መሆኑን በውል የምንገነዘበው ነው፡፡ ይህ ሕዝብ በአሁኑ ጊዜ በብዙ መልኩ እየተፈተነ ነው፤ ሕዝቡ በሰላም ዕጦት የኅሊና ጭንቀት ላይ ነው የሚገኘው፤ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በቀጣዮቹ ዓመታት በእጅጉ ሊጎዳ እንደሚችል የበሽታው ተጽዕኖ ምልክት እያሳየ ነው፤ የተከሠተው በሽታ መቼ ሊወገድ እንደሚችል የሚታወቅ ነገር የለም፤ ስለሆነም በዚህ ሁሉ ፈተና ተጎጂው ማን ነው? ሲባል እኛ እረኛ የሆንለት ሰፊው ሕዝብ በተለይም በዝቅተኛ ኑሮ የሚኖር ድሀው ሕዝባችነ ነው፡፡

ይህ ሕዝብ እየታዩ ባሉት ችግሮች በመከራ ቢለበለብ በእግዚአብሔር ዘንድ ያስጠይቀናል፤ ሕዝቡም ይታዘበናል፤ ይህም እንዳይሆን በተቻለ ዐቅም በጸሎትም፣ በትምህርትም፣ በምክርም፣ በማስታረቅም ሰፊ የማግባባትና የሕዝብ አድን ሥራ መሥራት አለብን፤ አሁን ያለው ጥያቄ ሀገርንና ሕዝብን ከፈተና የመታደግ ጥያቄ ነው፤ ይህንን ፈተና መሸጋገር የምንችለው በአንድነት ሆነን ስንቆም ብቻ ነው፤ አንድነትን ለማምጣት ደግሞ የማግባባት ሥራ የግድ መሥራት አለብን፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ይህ ጉባዔ በጥልቀትና በአጽንዖት ተወያይቶ ወደ ተጨባጭ ሥራ እንዲገባ ያስፈልጋል፡፡

ሕዝባችን በውስጣዊና አካባቢያዊ የአስተሳሰብ ልዩነት ምክንያት ብዙ ውጣ ውረድ ባለበት ወቅት ተጨማሪ ሸክም ሆኖ የመጣብንን የኮረና በሽታም በአጭር ታጥቀን ሕዝቡን በማስተማር፣ በጸሎት በመትጋትም ክፉውን ቀን በሰላም እንድናሸጋግረው ጠንክረን መሥራት አለብን፡፡ እስከ አሁን ድረስ ቤተ ክርስቲያናችን፣ ሌሎች አብያተ ሃይማኖት፣ መንግሥትና ሕዝብ፣ እንደዚሁም የተለያዩ የሚድያ አውታሮች በጋራ ሆነው በሠሩት ሥራ ቢያንስ የወረርሽኙ በሽታ የከፋ አደጋ እንዳያደርስ በመከላከላቸው በዚህ አጋጣሚ ሳናመሰግን አናልፍም ለወደፊቱም በዚሁ እንዲቀጥል በጋራ እየተባበሩ መሥራቱን ማጠናከር ይኖርብናል፡፡

በመጨረሻም፡ ሁላችንም እንደምናየውና እንደምንገነዘበው በሀገራችን እየተከሠቱ ያሉት የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግሮች ሁሉ መንግሥትና የፖለቲካ ተፎካካሪ ፓርቲዎች እግዚአብሔርና ታሪክ የጣለባችሁን አደራ በላቀ አስተውሎት ነገሩን በማጤን ሀገርንና ሕዝብን በሰላም፣ በጤና እና በአንድነት የማሻገር ከፍተኛ ኀላፊነት በእጃችሁ እንዳለ አውቃችሁ ይህንን ሕዝብና ሀገር ወደ ተሻለ አስተማማኝ ሰላም፣ ጤንነትና እድገት በፍቅርና በአንድነት ሁናችሁ እንድታሸጋግሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አደራ ትላችኋለች፡፡ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምን ጊዜም ከሕዝቡ ጎን መሆኑን እየገለጽን የሁለት ሺ ዐሥራ ሁለት ዓመተ ምሕረት የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባዔ በዛሬው ዕለት መከፈቱን እናበሥራለን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!