• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ግንቦት 14 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

May 19, 2019

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ወኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤
ሁሉን ያደረገ፣ የሚሳነው ነገር የሌለ፣ እግዚአብሔር አምላካችን ቅድስት የሆነችው በዓለ ትንሣኤውን በሰላም አክብረን፣ በርክበ ካህናቱ ዓመታዊ ቅዱስ ጉባኤ ተገናኝተን፣ የቤተ ክርስቲያናችንን ጉዳዮች ለመመልከት ስለሰበሰበን፣ ክብርና ምስጋና ለአምላካችን ይሁን!!
“ወናሁ ወሀብኩክሙ ሥልጣነ ትኪዱ ዲበ ዐቃርብት ወዲበ አራዊተ ምድር ወዲበ ኵሉ ኀይለ ጸላኢ ወአልቦ ዘይነክየክሙ እነሆ እባቡንና ጊንጡን ትረግጡ ዘንድ በጠላትም ኀይል ሁሉ ላይ ሥልጣንን ሰጥቻችኋለሁ የሚጐዳችሁም ምንም የለም” (ሉቃ 10፥19)፡፡

ይህ ሥልጣን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ሲኖዶስ የሰጠው ላዕላዊና መለኮታዊ ሥልጣን ነው፤ ሁላችንም እንደምንገነዘበው ይህ ቃል ለሁሉም ሐዋርያት በጥቅል የተሰጠ ሥልጣን እንጂ በተናጠል ለተወሰኑ ሐዋርያት የተሰጠ ሥልጣን አይደለም፤ ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የተሰጠ ሥልጣን መሆኑን የምናስተውለውም በዚሁ መንፈስ ነው፤ እያንዳንዱ ሐዋርያ በተሰማራበት ግብረ ተልእኮ በኀላፊነት የሚያከናውነው ተግባር እንኳ ቢኖር፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ የመነጨና ለእርሱም ተቃራኒ ያልሆነ እንደሆነም መገንዘብ አያዳግትም፤ ከጌታችን አስተምህሮ የምንገነዘበው በደሙና በቃሉ በምድር ላይ የመሠረታትን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጨርሰው ባያጠፏትም የሚታገሏት መናፍስት መኖራቸውን ነው፤ በእባብና በጊንጥ የተመሰሉትም ሰውን በፍቅረ ንዋይ፣ በፍቅረ ሢመትና በክፉ መንፈስ በማለያየት የሚመርዙ እነዚህ እኩያን መናፍስት ናቸው፤ ነገር ግን ምስጋና ለእግዚአብሔር ይድረሰውና እነዚህ እኩያን መናፍስትን ማሸነፍ የሚያስችል ልዩ ሥልጣንና ኀይል ጌታችን ለዚህ ቅዱስ ጉባኤ ሰጥቶአል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ የዘወትር ተግባር ኀይለ ሃይማኖትን፣ ኀይለ ጸሎትን፣ ኀይለ ቃለ ቅዱስ ወንጌልንና ጥብዐተ ልቡናን ተጠቅሞ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት እባቡንና ጊንጡን መርዝ አልባ እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡ ጌታችን “ያለ እኔ ምንም ምን ማድረግ አትችሉም” ብሎ እንዳረጋገጠልን፣ ይህንን ሥልጣን በአግባቡ መለማመድና መተግበር የሚቻለው እግዚአብሔርን ይዞ እንደሆነ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፤ በሃይማኖት ስፍራ ይቅርና በሌላውም በማናቸውም ስፍራ ቢሆን የኀይል ሁሉ ምንጭ እግዚአብሔር ነውና ይህንን ኀይል መጠቀም የግድ ይላል፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን እስካሁን ድረስ በአሸናፊነት የዘለቀችው እባቡንና ጊንጡን በኀይለ እግዚአብሔር ድል እያደረገች ነው፤ አሁንም ይህን ኀይል በአግባቡ ለመጠቀም ከሁሉ በፊት ጽንዐ ሃይማኖትን መያዝ ነው፣ ለልዩ ልዩ ኀላፊ ጥቅም መንበርከክ አይደለም እስከ መጥዎተ ርእስ የሚዘልቅ ራስ መካድን ያስፈልገናል፡፡ ይህ ሲሆን ኀይለ እግዚአብሔር በምልአት ያድርብንና ያን ጊዜ በአርኣያ እግዚአብሔር የተፈጠሩ ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ግዑዛን ፍጥረታት ሳይቀሩ ለተሰጠን ሥልጣን ይገዛሉ፡፡

ቀደምት ቅዱሳን አበው በዓመት ሁለት ጊዜ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲካሄድ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ሲደነግጉ እንዲሁ አልነበረም፤ የቤተ ክርስቲያን ሐዊረ ፍኖት ጸዊረ መስቀልና በፈተና የተሞላ በመሆኑ፣ በየጊዜው የሚያጋጥመውን ፈተና በትክክል በማጥናትና በመረዳት በተጠቀሰው ኀይለ ሥልጣን ለመመከት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ነው፤በዚህ ረገድ ቤተ ክርስቲያናችን ህልውናዋን ‹ጨርሶ እስከ ማጥፋት የተገዳደሩዋትን ፈተናዎች መሻገር የቻለችው ራስን ከመካድ እስከ መጥዎተ ርእስ በዘለቀ ጽኑ ሃይማኖት ነው፤ በአሁኑ ጊዜ በኀላፊነት የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስም እንደቀድሞዎቹ አባቶች እስከ መጥዎተ ርእስ የሚዘልቅ ብርቱ ጽንዐ ሃይማኖትን አንግቦ ቤተ ክርስቲያንን ለቀጣዩ ትውልድ ማሸጋገር ይጠበቅበታል፡፡

የዘመናችን ፈተና በአብዛኛው እንደቀድሞው በአዋጅ አስነግሮ፣ መሣሪያ ደግኖ፣ ጦር ሰብቆ፣ሰይፍ መዞ ላጥፋችሁ ብሎ የሚመጣብን ላይኖር ይችላል፤ ነገር ግን ውስጥ ውስጡን መርዝ ቀብቶ ላይ ላዩን ደግሞ ማር ለውሶ የሚመጣብንና በጐጂነቱም ከባለፈው የባሰ ሊሆን የሚችል መንፈስ ግን በዓለም እንዳለ በግልጽ እየተስተዋለ ነው፤ እነዚህ በርቀት እየተዋጉን ያሉ እባቦችና ጊንጦች ከእነሱ የበለጠ ረቂቅ ኀይልን ገንዘብ አድርጎ መመከት ያሻል፣ ነጋ ጠባ የምእመናን ፍልሰት፣ የመልካም አስተዳደር ዕጦት፣ የምጣኔ ሀብት አያያዝ ጒድለት፣ የቤተ ክርስቲያናችን አጀንዳ ሆነው መቀጠል የለባቸውም፤ “እነሆ እባቡንና ጊንጡን እንድትረግጡ ሥልጣንን ሰጥቻችኋለሁ፤ የሚጎዳችሁም የለም” የሚል እጅግ ረቂቅ ኀይለ ሥልጣን የተሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስ ከላይ የተጠቀሱትን ጉድለቶች ማረም ዐቀበት ሊሆነው አይገባም፡፡

ስለሆነም በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ የሚታዩ ወቅታዊ ችግሮች በጥቅል ሲታዩ ከተጠቀሱት ውጭ ስላልሆኑ፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ፍልሰተ ምእመናንን የሚገታ፣ መልካም አስተዳደርን የሚያሰፍን፣ ምጣኔ ሀብትን የሚያስጠብቅ አሠራር እውን እንዲያደርግ ሕዝበ ክርስቲያኑ በጒጉት እንደሚጠብቅ ግንዛቤ መወሰድ አለበት፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን ኀላፊነት ድርብ ኀላፊነት እንደመሆኑ መጠን ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያን ህልውና የሚጨነቀውን ያህል፣ ለሀገር ሰላምና አንድነትም የመጨነቅ ኀላፊነት እንዳለበት ሁላችንም እንገነዘባለን፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በሀገራችን እየተከሠተ ከሚገኘው መጠነ ሰፊ ችግር አንጻር፣ በተደጋጋሚ ምሕላና ጸሎት እንዲደረግ፣ የሰላምና የአንድነት አስተምህሮ በስፋት እንዲሰጥ፣ የዕርቅና የኀዲገ በቀል ልምድ እንዲሠርጽ፣ ሁሉም የሃይማኖት አባቶች በዚህ ዙርያ አጥብቀው እንዲሠሩ ከዚህ ቀደም መወሰኑ የሚዘነጋ አይደለም፡፡

ይሁን እንጂ በአክሱምና በሌሎች ጥቂት ገዳማትና አድባራት በዕንባና በልቅሶ የታጀበ ጸሎተ ምሕላ ቢደረግም፣ ከርእሰ ከተማው ከአዲስ አበባ ጀምሮ በብዙ ቦታ ጸሎተ ምሕላው ተጠናክሮ እንዳልተካሄደ ለማወቅ ተችሎአል፡፡ ይህም በመሆኑ መከራው ሊያጥር እንዳልቻለ፣ ይልቁንም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ እንደሆነ እያየን ነው፡፡ እንደ ቀደምት አባቶቻችን ከሕፃን እስከ ሽማግሌ፣ እንስሳትም ሳይቀር፣ ከእህልና ከውኃ ተለይተን በኀዘንና በዕንባ፣ በልቅሶና በንስሓ፣ ፈጣሪያችንን ብንማፀነው ኖሮ ሰላማችንንና አንድታችንን በአጭር ጊዜ እንደሚያረጋገጥልን ጥርጥር የለውም፡፡

ከዚህ አኳያ አሁንም ሁሉን ማድረግ የሚችለው፣ ምንም ምን የሚሳነው የሌለ፣ እግዚአብሔር አምላካችን ብቻ ነውና፣ እሱ በመሠረተልን ስልት “እጃችንን ወደ እግዚአብሔር እንድንዘረጋ” ሕዝቡም ሁሉ፣ ሀገሪቱም በአጠቃላይ “እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር እንድትዘረጋ” እኛም በየሀገረ ስብከታችን ተገኝተን፣ ራሳችን መሪዎች ሆነን ጸሎተ ምሕላውን እንድንመራ፣ ትምህርተ ወንጌሉን እንድንሰጥ፣ ቂም በቀል እንዲከስም ይቅርታ እንዲያብብ ያለማቋረጥ የሽምግልና ሥራን መሥራት ከሁላችን ይጠበቃል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ የሕዝቡ እረኛ እንደመሆኑ መጠን አባቶች ከሀገረ ስብከታቸውና ከሕዝባቸው ሳይለዩ ሕዝቡን ሊመሩ፣ ሊያስተምሩ፣ ሊያስታርቁና ሊያጽናኑ ይገባል፤ ሕዝቡም የአባቶችን ድምፅና ትምህርት፣ ምክርና ተግሣጽ በአክብሮት ተቀብሎ ሊፈጽም ይገባል፤ ሀገርንና ሕዝብን ለማገልገል በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኙ ተፎካካሪ ፓርቲዎችም ለግጭትና ለመለያየት በር ከሚከፍቱ ተግባራትና ቅስቀሳዎች ተቈጥበው የሀገር ሰላምና አንድነትን የጋራ አጀንዳ አድርገው፣ ችግሮችን ሁሉ በውይይትና በውይይት ብቻ ለመፍታት በቊርጠኝነት እንዲሠሩ፣ ኀይለ ቃል መጠቀምንና ስም ማጥፋትን እንዲያቆሙ፣ በዚህ አጋጣሚ በኀያሉ በእግዚአብሔር ስም መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

የዘንድሮ የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የሚከናወነው፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ለዓመታት በአቤቱታ የደከመባቸውንና በጽ/ቤታችን አጠገብ የሚገኙትን ሁለት ታላላቅና ሁለት መለስተኛ የቤተ ክርስቲያናችን ሕንጻዎች፣ የኤፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ መመለሳቸውን ባበሠሩንና ባረጋገጡልን ማግስት በመሆኑ፣ ጉባኤውን ከሌላው ጊዜ ልዩ ያደርገዋል፡፡ በዚህ አጋጣሚ የቤተ ክርስቲያናችንን የዓመታት አቤቱታ ከልብ አጢነውና ተቀብለው ሕንጻዎቻችን እንዲመለሡልን ያደረጉ እና ጥያቄያችንን የመለሱ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችንንና መንግሥታችንን በቤተ ክርስቲያናችን ስም ከልብ እናመሰግናቸዋለን፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና መላው ሕዝበ ክርስቲያንም እንኳን ደስ አላችሁ እንላለን፡፡

በመጨረሻም፡ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ህልውና፣ እንደዚሁም ስለ ሀገራችን ሰላምና አንድነት በየዓመቱ ሁለት ጊዜ እየተሰበሰበ በመገምገም ወሳኝ የሆኑ ውሳኔዎችን የሚያስተላልፈው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዛሬ ግንቦት 14 ቀን 2011 ዓ.ም. በጸሎት የተከፈተ መሆኑን እናበሥራለን፡፡ እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ ይቀድስ እንደዚሁም ኢትዮጵያ ሀገራችንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32019-05-19 09:27:052025-01-27 09:29:22ግንቦት 14 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ሚያዝያ 20 ቀን 2011 በዓለ ትንሣኤ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ሚያዝያ 20 ቀን 2011 በዓለ ትንሣኤ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሚያዝያ 20 ቀን 2011 በዓለ ትንሣኤ ቃለ ምዕዳንና ... Link to: ከግንቦት 14 ቀን እስከ ሰኔ 3 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከግንቦት 14 ቀን እስከ ሰኔ 3 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከግንቦት 14 ቀን እስከ ሰኔ 3 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top