• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

October 22, 2018

የመጀመሪያው የአንድነት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ

የጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም ምልአተ ጉባኤ ለየት ያለ ነበር፡፡ ምንም እንኳ በአራተኛው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ወደ ሀገራቸው መግባት ማግስት ሲኖዶሳዊ ትውውቅ የተደረገ ቢሆንም በዚህ ዓለም ዐቀፍ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የመጀመሪያው የአንድነት የሲኖዶስ ጉባኤ ተደርጓል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የምልአተ ጉባኤ መከፈትን አስመልክተው የሚከተለውን አባታዊ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላለፈዋል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ራብዓይ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ወኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ባለችው ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያናችን፣ ሃይማኖታዊ አገልግሎታችንን እየባረከ ዘወትር ከእኛ የማይለይ እግዚአብሔር አምላካችን፣ አሁንም ለበለጠ ሐዋርያዊ ሥራ እንድንመካከር በስሙ ስለ ሰበሰበን ስሙ የተመሰገነ ይሁን፡፡

በቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ በዓለም ዐቀፍ ክርስቲያናዊ አስተምህሮ እንደሚታወቀው፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ መሠረቱ ክርስቶሳዊ አስተምህሮ፣ሐዋርያዊ ትውፊትና ቀኖና ቅዱሳን አበው ነው፡፡

ክርስቶስ መድኀኒታችን “በስሜ በምትሰበሰቡበት እኔ በመካከላችሁ እኖራለሁ” ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶአል፤ ይህን ተከትሎም የመጀመሪያው ሲኖዶሳዊ ጉባኤ በቅዱሳን ሐዋርያትና በቀሲሳን ኅብረት በቅድስት ሀገር በኢየሩሳሌም ማእከላዊነት፣ በቅዱስ ያዕቆብ እኁሁ ለእግዚእነ ርእሰ መንበርነት፣ በዘመነ ሐዋርያት እንደተካሄደ “ወአንገለጉ ሐዋርያት ወቀሲሳን ከመ ይርአዩ ዘይገብሩ በእንተዝ ነገር፣ ሐዋርያትና ቀሳውስትም ስለዚህ ነገር ለመመካከር ተሰበሰቡ” ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ ተመዝግቦአል፡፡ የተወሰነው ውሳኔም መንፈስ ቅዱስ ያለበት መሆኑን ለማመልከት “እኛና መንፈስ ቅዱስ ፈቅዶናል” ተብሎ ተገልጾአል፡፡ (የሐ.ሥራ 15፤6-29)፡፡

ከዚህ ጊዜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ያጋጠሙ ፈተናዎችን ለማየት፣ ላለፈው እርማትና ማስተካከያን ለመስጠት፣ ለሚቀጥለው የሥራ አቅጣጫን ለማስቀመጥ፣ ተላውያነ ሐዋርያት በየጊዜው ሲኖዶሳዊ ጉባኤ ያካሂዱ እንደነበር ሁላችንም የምናውቀው ነው፤ በተለይም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዓለ ቅዱስ መስቀል በተከበረ በሃያ አምስተኛው ቀን ጥቅምት ዐሥራ ሁለትና የትንሣኤ በዓል በዋለ በሃያ አምስተኛው ቀን ርክበ ካህናት በድምሩ በዓመት ሁለት ጊዜ እንዲካሄድ በቀኖና ቤተክርስቲያን መደንገጉ በፍትሕ መንፈሳዊ ተጽፎ ይገኛል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ዋና ዓላማ ቤተ ክርስቲያን ከዐላውያን፣ ከአረማውያንና ከከሐድያን በየጊዜውና በየአቅጣጫው የሚሰነዘርባትን ጥቃት በሃይማኖት ጽናት ለመቋቋም፣ በድንበር፣ በወንዝ፣ በባሕር፣ በየብስ፣ በዘር፣ በጎሳ፣ በፆታ፣ በቀለም፣ በሀብት፣ በሥልጣን፣ በዕውቀት፣ በጒልበት፣ ወ.ዘ.ተ ሳትገደብ መንግሥተ እግዚአብሔርን በዓለም ዙሪያ ሁሉ ለመስበክ፣ ለምእመናን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎትን ለማበርከት፣ በሰው ልጆች መካከል እኩልነት፣ሰብአዊነትና ፍትሕ እንዲሰፍን የበኩሏን አስተዋፅኦ ለማድረግ እንድትችል ነው፡፡

ሐዋርያዊት፣ ዓለም አቀፋዊት፣ አንዲትና ቅድስት የሆነችው ቤተ ክርስቲያናችን የክርስቶስን አስተምህሮ፣ የቅዱሳን ሐዋርያትና የቀደምት ቅዱሳን አበውን ፈለግ ተከትላ፣ እነኝህን ዐላማዎች በመፈጸም ለሁለት ሺሕ ዘመናት ያህል ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ስታገለግል ኖራለች፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ጥንታዊውን የሐዋርያት ትውፊት፣ቀኖና እና ሥርዐት ጠብቃ በማስጠበቅ ያልተበረዘ፣ ያልተከለሰና ያልተሸራረፈ ሃይማኖታዊ አስተምህሮን በመከተል በዓለም ውስጥ የተዋጣላት ብቸኛዋ ቤተ ክርስቲያን እንደሆነች ሁሉም የዓለም ክርስቲያኖችና ተመራማሪዎች ያረጋገጡት እውነት ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን በምትከተለው ጥንቁቅ አስተምህሮና የማይናወጽ ጽንዐ ሃይማኖት ለሀገሪቱ አንድነትና ነፃነት፣ የግልዋ መለያ ለሆኑ ባህላዊ፣ ቍሳዊና መንፈሳዊ ቅርሶች መጠበቅ የአንበሳውን ድርሻ ወስዳ እስከ ዛሬ በድል ለመዝለቅ የቻለች ብቸኛ ኀያል እርስዋ እንደሆነች ማንም አይክደውም፤ ቤተ ክርስቲያናችን ይህ ጽናቷ በአፍሪካ ክፍለ ዓለምና በኦሪየንታል አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የቊጥር አንድ ደረጃን፣ በአጠቃላይ በኦርቶዶክሱ ዓለም ደግሞ በታሪክና በዶግማ ባይሆንም በቊጥር ብቻ ከሩስያ ቤተክርስቲያን ቀጥላ የቊጥር ሁለት ደረጃን ይዛ ትገኛለች፣ ይህ ጥንካሬና ጸጋ በቀደምት ኢትዮጵያውያን ተጋድሎ የተገኘ ደማቅና አኵሪ ታሪክ መሆኑን ኦርቶዶክሳውያን ብቻ ሳይሆኑ መላ ኢትዮጵያውያን ሊያውቁት፣ ሊኰሩበት፣ ሊንከባከቡትና ሊጠቀሙበት የሚገባ የጋራ ሀብት ነው፡፡ ምክንያቱም ሁሉም ኢትዮጵያውያን በዚህ ሀብተ ጸጋ ሲጠቀሙ ኖረዋል፣ አሁንም እየተጠቀሙ ነውና፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ካህናትና ምእመናንም ይህንን ሐቅ ለኢትዮጵያውያን ሁሉ የማሳወቅ ኀላፊነት ስላለባቸው በዚህ ዙሪያ በሰፊው ሊሠሩበት እንደሚገባ ሳንመክር አናልፍም፡፡

የዘንድሮ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ልዩ የሚያደርገው፣ ቤተ ክርስቲያናችን ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በአግባቡ እንዳትወጣ ዕንቅፋት ሆኖ የቆየው የመለያየት ጠንቅ ተወግዶ፣ በምትኩ አንድነትዋ ገሃድ ሆኖ በምሕረተ እግዚአብሔር በተጐበኘችበት ወቅት ላይ የሚካሄድ ጉባኤ መሆኑ ነው፡፡ ይህ ዕድል በመልካም ጎኑ የምንመለከተው ሆኖ፣ በተቃራኒው ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችን በከፋ መልኩ የተደፈረችበት፣ ካህናቶቻችንና ምእመናን ልጆቻችን ለሰው ኅሊና በሚከብድ ድርጊት በአሠቃቂ ጭካኔ የሰማዕትነትን ጽዋ በተቀበሉበት ማግስት የሚካሄድ ጉባኤ መሆኑ ልዩ ያደርገዋል፡፡

በመሆኑም ከዐሥር ዓመታት በፊት በጂማና በኢልባቦር አህጉረ ስብከት፣ በጉራጌና በአርሲ ነገሌ፣ በቅርቡም በባሌ ተቃጥቶ በነበረው አደገኛ ሙከራ፣ ከሁሉም የባሰ ደግሞ በኢትዮጵያ ሶማሌ ሀገረ ስብከት የተፈጸመው ጣራ የነካ ግፍና ጭካኔ፣ እልቂትና ውድመት ቤተ ክርስቲያናችንን ክፉኛ የጎዱና የተዳፈሩ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ችግሩ ወደሌሎችም እንዳይስፋፋና የከፋ ጉዳትን እንዳያስከትል በከፍተኛ የኀላፊነት ስሜት ኀዘንዋን በልብዋ አምቃ ለማለፍ ብትሞክርም፣ ድፍረቱ ከቀን ቀን እየባሰ፣ ዕልቂቱም እየጨመረ፣ ተጽዕኖው እየተባባሰ በመሄዱ ልትታገሠው ከማትችልበት ደረጃ እየደረሰ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያውያን ሁሉ በፊደልዋ ማዕድ ዕውቀትን እየመገበች፣ በታቦትዋ አዝማችነት ለነፃነትና ለወገን ክብር መተኪያ የሌለው መሥዋዕትነትን እየከፈለች፣ የሁሉም እምነቶች ነጻነት ሳትጋፋ፣ አንዱን ስንኳ ሳትጫንና ክብሩን ሳትነካ በሺሕ ለሚቈጠሩ ዘመናት እንዳልዘለቀች ሁሉ፣ ዛሬ በኢትዮጵያውያን ወገኖችዋ ስትቃጠል ማየት አሳፋሪና የድፍረት ድፍረት ነው፤ የቤተ ክርስቲያናችን ተከታይ ምእመናንና አገልጋይ ካህናት በነፃ የማስተማር፣ የማምለክና የመኖር ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን በሚቃረን አኳኋን በሚደርሳቸው ተጽዕኖ ከቀያቸው እየተፈናቀሉ እንዲወጡና ሃይማኖቱ እንዲዳከም የሚደረጉ ደባዎች እየተበራከቱ ነው፡፡

ይህ ሁሉ እየሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ ለካህናትና ለምእመናን አስተማማኝ የሆነ መፍትሔ አበጅቶ ዘላቂ ዋስትና የማያረጋግጥ ከሆነ በታሪክና በእግዚአብሔር ዘንድ ተወቃሽ መሆኑ አይቀርም፤ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ ይህ መሰሉ ችግር ተወግዶ ካህናትና ምእመናን ያለምንም ተጽዕኖና ሥጋት በነፃነት ሥርዐተ አምልኮአቸውን የሚፈጽሙበትና የመኖር መብታቸው የሚከበርበት ድባብ ለመፍጠር በየአካባቢው ጠንካራ የግንኙነት መረብ ዘርግቶ የቅድመ ትንበያ ሥራ በመሥራት፣ እንደዚሁም ከፍትሕና ከፀጥታ አካላት ጋር በቅንጅት በመሥራት፣በቤተ ክርስቲያንና በአማንያን የሚሰነዘረውን ጥቃትን አስቀድሞ ማምከን የሚቻልበትን አሠራር መቀየስ የግድ ይላል፡፡

ከዚህም ሌላ የቤተ ክርስቲያናችንን አስተዳደር ክፉኛ እያስተቸ የሚገኘው የመልካም አስተዳደር ዕጦት፣ የሀብት አያያዝ ክፍተት፣ የምእመናን ፍልሰት፣ የተልእኮ ሐዋርያት አለመጠናከር፣ በውጭም በውስጥም ከቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውጭ በግላቸው አስተዳደራዊ መዋቅርን ከላይ እስከ ታች እየዘረጉ ቤተ ክርስቲያንን የሚጋፉ ልዩ ልዩ ማኅበራት፣ቀኖና ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅደው መሠረት በሕግ፣ በመሪ ዕቅድ፣ በፖሊሲ፣ በደንብና በመመሪያ መልክን እያስያዙ የቤተ ክርስቲያንን ሉዓላዊነት፣ አንድነት፣ ክብርና መብት መጠበቅ ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ ሆኖ ይገኛል፡፡

ከዚህም ሌላ ያለንበት ወቅት ሀገራችን በብሩህ ተስፋና በሥጋት መንታ መንገድ ላይ የቆመችበት ጊዜ እንደሆነ በግልጽ የሚታይ ነው፡፡ በመሆኑም ሥጋቱ ተወግዶ ብሩህ ተስፋው ብቻ እንዲፈነጥቅ ቀጣዩ ዘመን ለሕዝባችን ወንድማማችነትና እኩልነት፣ለሀገር አንድነትና ለዜጎች ደኅንነት ያለዕረፍት ድምፃችንን ከፍ አድርገን የምንሰብክበት፣ከማንም የፖለቲካ ርእዮት ገለልተኛ በመሆን በአስታራቂነት ብቻ የምንቆምበት ጊዜ አሁን እንደሆነ መገንዘብ ይኖርብናል፡፡

እኛ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች፣ ካህናት፣ መምህራንና ሰባክያን የሁሉም ፖለቲከኞች አባቶች መሆናችንን ዐውቀን፣ ሁሉንም በአባትነት መንፈስ መመልከት፣ ማስተማርና መምከር እንጂ አንዱን አገልግሎ ሌላውን አቅርቦ ማየት ከሃይማኖት አስተምህሮ ጋር የማይሄድ ስለሆነ ልንጠነቀቅበት ይገባል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን አጠቃላይ አሠራር የዘመነና የሠለጠነ፣ ግልጽነትንና ተአማኒነትን ያሰፈነ፣ በልጆቻችን ምእመናን ዘንድ አድናቆትን፣ተቀባይነትንና ይሁንታን ያተረፈ እንዲሆን ለማድረግ ሁሉን የቤተ ክርስቲያን ሥራዎች ያካተተ፣ ጥልቅና ችግር ፈቺ የሆነ፣ ሰፊና ለረጅም ጊዜ የሚያገለግል መሪ ዕቅድ የሚዘጋጅበት መደላድል መፍጠር አለብን፣ ይህም ጊዜ ሳይወስድ በፍጥነት ተሠርቶ ለቀጣዩ ስብሰባ እንዲቀርብ ዛሬ መወሰን ይኖርብናል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን የተዋጣለት መሪ ዕቅድ ሲኖራት፣ በእርግጠኝነት ሁሉንም ችግሮች ተቋቁመን የተሻለ ልማትና እድገትን በሁሉም አቅጣጫ እናስመዘግባለን፣ የምንጓዝበት ፍኖተ ምሕዋርና የምንደርስበት ጫፍም በትክክል ማወቅ እንችላለን፤ ፈጣን የሆነ ሐዋርያዊ፣ መንፈሳዊ፣ አስተዳደራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትንም እናስመዘግባለን፤ ስለሆነም የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደራዊ ችግርን መፍታት የምንችለው በመሪ ዕቅድ በመመራትና መልካም አስተዳደርን በማበልፀግ እንደሆነ፣ ከዚህ ውጭ ግን ሌላ አማራጭ ሊኖር እንደማይችል መገንዘብ ይኖርብናል፤ ሌላው በዚህ ጉባኤ ሳናነሣው የማናልፍ ዐቢይ ነጥብ የኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ነው፤ የታሪክ አጋጣሚና የትውልድ ዕድል ጉዳይ ሆኖ አሁን ላለንበት ሁኔታ ብንዳረግም ከኢትዮጵያ የተነጠለ የኤርትራ ታሪክ፣ ከኤርትራ የተነጠለ የኢትዮጵያ ታሪክ ፍጹም እንደሌለ እኛ ብቻ ሳንሆን ዓለም በሙሉ የሚያውቀው ሐቅ ነው፡፡

ከጅምሩም ግራና ቀኛችን በሚገባ አርቀን ካለማየታችን የተነሣ ለጊዜው ተለያይተን ቆየን እንጂ የሚለያየን ሃይማኖታዊም ሆነ ቀኖናዊ ምክንያት የለንም፤ ምድራዊ መንግሥት በፖለቲካ ምክንያት ቢለይም እንኳ፣ ለሃይማኖት ድንበር ስለሌለው በአንድነት እየተደጋገፍን መቀጠል ይገባን ነበር፡፡ ይህ እውነታ ለእኛ ለኦርቶዶክሳውያኑ ባያድለንም፣ ሌሎች መሰል አብያተ ክርስቲያናት ግን እስካሁን ጠብቀውት እንዳለ ማየት እንችላለን፤ ነገር ግን “ላለፈው ክረምት ቤት አይሠራም” እንደሚባለው ያለፈውን ለታሪክ ትተን፣ ለወደፊቱ ተጋግዘን፣ ተረዳድተንና ተደጋግፈን፣ የጋራችን የሆነ ሃይማኖትን፣ ታሪክና ባህልን ጠብቀን በማስጠበቅ ኦርቶዶክሳዊውን ሕዝብ ማገልገል እግዚአብሔርና ታሪክ የጣሉብን አደራ መሆኑን መገንዘብ አለብን፡፡

እውነቱን ለመናገር ለኢትዮጵያ ምእመናን ከኤርትራ ምእመናን፣ ለኤርትራ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የበለጠ የክፉ ቀን ደራሽ የላቸውም ፣በመሆኑም በሁሉም ሃይማኖታዊ የሥራ መስክ ተቀራርቦ ለመሥራት ቅዱስ ሲኖዶስ ዝግጁነቱን መግለጽ ይኖርበታል፤ በሁለቱም አብያተ ክርስቲያናት የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖር የጋራ ኮሚሽን አቋቁመን መንቀሳቀስም ይገባናል፡፡

በመጨረሻም፤ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ከላይ በዝርዝር የተጠቀሱትን አንገብጋቢ የአገርና የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮችን አንድ በአንድ ተመልክቶና በጥልቀት መርምሮ አገራችንንና ቤተ ክርስቲያናችንን የሚጠቅሙ ውሳኔዎችን ያሳልፍ ዘንድ፣ እንደዚሁም የቤተ ክርስቲያናችን የቀደመው ክብርና ሞገስን፣ ሉዐላዊነትና አንድነትን ጠብቆ ያስጠብቅ ዘንድ ከማሳሰብ ጋር የጥቅምቱን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በጸሎት መከፈቱን በእግዚአብሔር ስም እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ጉባኤያችንን ይባርክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿንም ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32018-10-22 09:17:222025-01-27 09:21:00ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: 37ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት 5 ቀን 2011 ዓ.ም አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to: 37ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት 5 ቀን 2011 ዓ.ም አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ 37ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት... Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top