• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ሚያዝያ 12 ቀን የ2006 ዓ.ም በዓለ ትንሣኤ

April 20, 2014

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትኖሩ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፤

እርሱ ሕያው ሆኖ ሕያዋን መሆናችንን በትንሣኤው ላበሠረን ለጌታችን ለአምላካችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤ እንኳን በሰላም አደረሳችሁ!! ‹‹ወርኢናሃ ለሕይወት፤ ወተዐውቀት ለነ — ሕይወትን አየናት፣ አወቅናትም›› (1ዮሐ. 1÷2)

የሕይወት መገኛና ምንጭ አምላካችን እግዚአብሔር ነው፣ ከእግዚአብሔር የተገኘው ሕይወት የሰው ልጅ የዕውቀት ብርሃን ነው፤ አምላካዊ ሕይወት ካለው ሰው የሚፈልቅ ብርሃናዊ ዕውቀት ጽልመታዊውን ዓለም በብሩህነቱ ያሸንፋል እንጂ በጽልመታዊ ዓለም አይሸነፍም፡፡ (ዮሐ.1÷4-5) የሰው ልጅ ሕያው አምላክ በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረው ፍጡር በመሆኑ ሕያውና ክቡር፣ ዘለዓለማዊና ብርሃናዊ፣ የማሰብ፣ የማመዛዘን፣ የመምረጥና፣ የመወሰን ነፃነት ያለውና ከሌሎች ፍጥረታት ሁሉ የላቀ አእምሮ ያለው ልዑል ፍጡር ነው፤ ሰው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ነፃነትና አእምሮ መሠረት ነፃነቱን ተጠቅሞ የመረጠውን የማድረግ ነፃነት ያለው ፍጡር ቢሆንም በነፃ ዕውቀቱና ምርጫው ለሚፈጽመው ሁሉ እርሱ ራሱ ኀላፊነቱን ይወስዳል፤ ይህም ማለት በምርጫው መሠረት የሚሠራው ሥራ ሁሉ በእውነተኛው ዳኛ በእግዚአብሔር ፊት መልካም ሆኖ ከተገኘ ምስጋናን፣ መልካም ሆኖ ካልተገኘ ግን ተጠያቂነትንና ፍርድን ያስከትልበታል ማለት ነው፡፡

ከዚህ አንጻር የመጀመሪያ ሰው የሆነው አዳም ማድረግ ያለበትንና ማድረግ የሌለበትን ተለይቶ ከእግዚአብሒር ቢነገረውም የተነገረውን ሕግ ወደጎን ገሸሽ በማድረግ የራሱን ነፃ ምርጫ ተጠቅሞ ‹‹አትብላ›› የተባለውን በላ፤ በመሆኑም ይህ ድርጊት በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ ታላቅ ስሕተትና ድፍረት ነበረና ተጠያቂነትን አስከተለ፣ በመጨረሻም ሕይወትን የሚያሳጣ የሞት ፍርድንና ቅጣትን በራሱና በልጆቹ ሁሉ ላይ አመጣ፡፡ ፍርዱ ሥራ ላይ ከዋለበት ቀን ጀምሮ ሰው ሕይወቱን አጣ ማለትም ከእግዚአብሔር አንድነት ተለየ፤ ሞትና ሲኦልም ሰውን ከእግዚአብሔር ለይተውና የራሳቸው ተገዥ አድርገው እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ድረስ በቊጥጥራቸው ሥር አዋሉት፡፡ ሆኖም እግዚአብሔር በባሕርዩ መሓሪና ፈራጅ እንደመሆኑ መጠን ለፈራጅነቱና ለመሓሪነቱ የሚስማማ መንገድ አመቻችቶ መሓሪነቱንና ፈራጅነቱን በፈጸመበት በክርስቶስ ሞት ቤዛነት የሰው ልጅን ታረቀው፤ ያጣውንም ሕይወት መለሰለት፤ በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አማካኝነትም እንደገና ሕይወቱን እንዲያገኝ አደረገ (ዮሐ. 6÷56-58፤ ማር 16÷16)

ይህን አስመልክቶ ቅዱስ ጳውሎስ ሲናገር‹‹በመጀመሪያው ሰው (አዳም) ሞት መጣ፣ በሁለተኛው ሰው (ክርስቶስ) ግን ትንሣኤ ሙታን ሆነ፤ሁሉም በአዳም እንደሚሞቱ እንደዚሁ ሁሉም በክርስቶስ ሕያዋን ይሆናሉ›› ብሏል፤ (1ቆሮ. 15÷21-22፤ሮሜ 5፥12-19) ከዚህ የምንረዳው ዐቢይ ቁም ነገር በአዳም አለመታዘዝ ምክንያት ያጣናት ሕይወት፣ በክርስቶስ መታዘዝ ያገኘናት መሆናችንን ነው፤ ጌታችንም ‹‹ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም፣ የሚያምንብኝም፣ ሁሉ ለዘለዓለም አይሞትም፤እኔም በመጨረሻዪቱ ቀን አስነሣዋለሁ›› ብሎ ትንሣኤና ሕይወት መሆኑን እንደነገረን የሰው ልጅን ለዘለዓለማዊ ሕይወት እንደገና አበቃው (ዮሐ. 6÷54፤ 11÷25-26)። የዚህም እውነታ በትንሣኤው አበሠረን፣ የእርሱ ትንሣኤ የትንሣኤያችን ዋዜማ ነውና የቀደመችው ሕይወት እንደተመለሰችልን በትንሣኤው አየናት፤ ዐወቅናትም። (ኤፌ. 4÷5-7)

የክርስቶስ ትንሣኤ ለሰው ልጅ የዘለዓለማዊ ሕይወት ማረጋገጫ ነው፤ለበርካታ ዘመናት በተስፋ ይጠበቅ የነበረው የክርስቶስ ነገረ አድኅኖ እና ነገረ ትንሣኤ በጊዜው ጊዜ እውን እንደሆነ ሁሉ፣ እንደዚያው በተስፋና በእምነት እየተጠባበቅነው ያለ የሰው ልጅ ሕይወታዊ ትንሣኤ ጊዜው ሲደርስ በክርስቶስ ዳግም ምጽአት እውን ይሆናል (1ቆሮ 15÷20-23፤ 1ተሰ. 4÷13-18)። ይሁን እንጂ ዛሬም ሕይወትን በሚሰጥ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ያለን ስለሆን የሕይወትን ጣዕም አሁንም ማጣጣም እንችላለን፤ ሕይወት ጣዕም የሚኖረው በፍቅር ሲታጀብ ነው፣ ፍጹም ፍቅር የዘለዓለማዊ ሕይወት ኀይል ነው፤ ፍቅር ፍጹም የሚሆነው ሦስቱን አቅጣጫዎች ማእከል አድርጎ ሲገኝ ነው፤ ይኸውም ወደ ላይ እግዚአብሔርን በፍጹም ፍቅር መከተል ስንችል፣ ወደጎን በአርኣያ እግዚአብሔር የተፈጠረውን የሰው ልጅ በአጠቃላይ መውደድ ስንችል፣ ወደ ታች ደግሞ የምንኖርባትን ምድርና በውስጧ ያሉ ፍጥረታትን ስንንከባከብ ነው፣ ይህን ካደረግን ፍጹም ፍቅር ከእኛ አለ ማለት እንችላለን፤ እግዚአብሔር ይህንን ዐይነት ፍቅር እንዲኖረን በሃይማኖት አስተምሮናል፡፡

በመሆኑም እኛ ክርስቲያኖች ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር ለመግለጽ በመዋዕለ ጾሙ በአምልኮ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋትና በስግደት ስንገልጽ እንደቆየን ሁሉ፣ በፋሲካው በዓላችን እግዚአብሔር የሰጠንን በረከት ከተቸገሩ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን ጋር በመካፈል ለወገኖቻችን ያለንን ፍቅር ልንገልጽ ይገባናል፤ በዚህ ዕለት በዓሉን ስናከብር የተራቡትን በማብላት፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ የታረዙትን በማልበስ፣ ጧሪ የሌላቸው አረጋውያን፣ አሳዳጊ የሌላቸው ሕፃናት፣ በልዩ ልዩ ምክንያት የአካልና የአእምሮ ጒዳት ደርሶባቸው የበይ ተመልካች የሆኑ ወገኖች ሁሉ ከእኛ ጋር በማዕዳችን ተሳታፊ ሆነው በዓሉን በደስታና በምስጋና እንዲያከብሩ ማድረግ ክርስቲያናዊ ግዴታችን ነው፡፡

የትንሣኤ መሠረታዊ ትርጒም ከሞት በኋላ በሕይወት መኖርና መመላለስ ነው፤ ስለሆነም የትንሣኤን በዓል ስናከብር ባለፉት ዘመናት በድህነትና በኋላ ቀርነት ከሞት አፋፍ ደርሳ የነበረችውን ሀገራችን በልማትና በእድገት ትንሣኤዋን ለማረጋገጥ ቃል በመግባት በዓሉን ማክበር ሀገራዊ ብቻ ሳይሆን ሃይማኖታዊ ግዴታ መሆኑን መገንዘብ አለብን፤ ምክንያቱም ጠንክረን በመሥራት ምድራችንን እንድናለማና እንድንከባከብ ከሁሉ በፊት ያዘዘ እግዚአብሔር ነውና፤ በተለይም የልማታችን የጀርባ አጥንት ሆኖ እንደ ሚያገለግል ታላቅ ተስፋ የተጣለበት ታላቁ የሕዳሴ ግድብ በተያዘው ፍጥነት ሥራው ተሠርቶና ተጠናቅቆ የእድገታችን ተሸካሚ ምሶሶ ሆኖ ማየት እንድንችል ሁሉም ኢትዮጵያዊ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ቤተ ክርስቲያናችን ጥሪዋን ታስተላልፋለች።

የሀገራችን የልማትና የእድገት መርሐ ግብሮች ዘርፈ ብዙ እንደመሆናቸው መጠን ገበሬው በየአካባቢው እያከናወነው የሚገኝ አፈርን የመገደብና አካባቢን በአረንጓዴ ልማት የማስዋብ ሥራ ያለመቋረጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በማድረግ ረገድ ቤተ ክርስቲያችን በግንባር ቀደም ተሰልፋ እንደምትሠራ በዚህ አጋጣሚ ለማረጋገጥ እንወዳለን፡፡ በአሁኑ ጊዜ በሥራ ላይ ያሉም ሆኑ ወደፊት ሊሠሩ በእቅድ የተያዙ የሀገራችን የልማትና የእድገት ሥራዎች በሕዝቡ የተባበረ ድጋፍ ሲከናወኑ የሀገራችን ብልጽግና እውን እንደሚሆን የሁላችንም እምነት ነው፡፡

ስለሆነም ለዚህ ስኬት የኢትዮጵያውን ሁሉ ጽናት፣ አንድነት፣ ስምምነትና ፍቅር፣ ሰላምና ተቻችሎ መኖር የማይተካ ሚና እንዳላቸው ለአፍታ እንኳ መዘንጋት የለብንም፤ ልማታችን በተፈጥሮ ሀብት እንክብካቤ ብቻ ሳይሆን የተቀደሰውና የተከበረው ባህላችንና ሰብኣዊ ሥነ ምግባራችንን ጠብቆ በማስጠበቅ ጭምርም መሆን ይገባዋል፡፡ ኢትዮጵያ ሀገራችን ከጥንት ጀምሮ በቅዱሳት መጻሕፍት ሀገረ እግዚአብሔር ነች ተብሎ በተደጋጋሚ የተነገረላት ያለምክንያት አልነበረም ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን በማናቸውም ጊዜ ከነውረ ኀጢአትና ከርኵሰት ሁሉ ርቀው፣ ሕገ ተፈጥሮንና ሕገ እግዚአብሔርን ጠብቀው፣ እግዚአሔር የሚለውን ብቻ አዳምጠውና አክብረው የሚኖሩ ቅዱሳን በመሆናቸው እንጂ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ምድር ሊፈጸም ቀርቶ ሊወራ የማይገባውን ሰዶምንና ገሞራን በእሳት ያጋየ ግብረ ኀጢአት በኢትዮጵያ ምድር መሰማቱ እግዚአብሔር ለኢትዮጵያውያን የሰጠውን የቅድስና ክብር የሚያሳጣ ከመሆኑም ሌላ በሀገራችን ላይ ልማትና እድገት ሳይሆን መቅሠፍትና ውድቀት እንዳያስከትልብን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ይህንን የሰዶም ግብረ ኀጢአት በጽናት መመከት አለበት፤ ተፈጥሮን ለማልማት እየተረባረብን እንደሆነ ሁሉ ከዚህ ባልተናነሰ ሁኔታ የሰዶም ግብረ ኀጢአትን በመከላከል በቅዱስ ባህልና ሥነ ምግባር እጅግ የበለጸገና የለማ ትውልድ ማፍራት የልማታችን አካል ማድረግ አለብን፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህንን ግብረ ኀጢአት እስከ መጨረሻው ድረስ አምርራ የምትዋጋው መሆኑን በዚህ አጋጣሚ ለመላው ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ማረጋገጥ እንፈልጋለን፤ ስለሆነም ሕዝባችን ለሰላምና ለአንድነት፣ ለእኩልነትና ለልማት፣ ለቅዱስ ባህልና ሥነ ምግባር ቅድሚያ ሰጥቶ በሁሉም አቅጣጫ ልማቱን እንዲያፋጥን፣ ሃይማኖቱንም እንዲጠብቅ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

መልካም የትንሣኤ በዓል ያድርግልን፤
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ ይቀድስ፤ አሜን።

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc2014-04-20 10:30:212024-12-05 10:31:28ሚያዝያ 12 ቀን የ2006 ዓ.ም በዓለ ትንሣኤ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: የካቲት 16 ቀን የ2006 ዓ.ም ዐቢይ ጾምን አስመልክቶ ያስተላለፉት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: የካቲት 16 ቀን የ2006 ዓ.ም ዐቢይ ጾምን አስመልክቶ ያስተላለፉት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የካቲት 16 ቀን የ2006 ዓ.ም ዐቢይ ጾምን አስመልክቶ... Link to: ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top