ግንቦት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
ቅዱስነታቸው ከተሾሙ በኋላ የመጀሪያው የርክበ ካህናት ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዐት ላይ የሚከተለውን ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል፡፡
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤
ምስጋና የባሕርዩ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ሁላችንንም ከየሀገረ ስብከቱ አሰባስቦ በዚህ ሐዋርያዊ፣ ቀኖናዊና ዐቢይ ጉባኤ ተገናኝተን ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ለመወያየት ስለፈቀደ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡ እንደዚሁም በዚህ ዐቢይ ጉባኤ ለመገኘት ከቅርብም ከሩቁም የመጣችሁ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሁላችሁም እንኳን በደኅና መጣችሁ፡፡
‹‹አስተጋብአተነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ሐዋርያት፤ ኀበ ሀለዉ አግብርተ እግዚአብሔር – ሐዋርያት የሰበሰቧት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር አገልጋዮች ወደአሉበት ሰበሰበችን› (ቅዱስ ያሬድ)፡፡
ሁላችንም እንደምናውቀው እዚህ ቅዱስ ስፍራ የሰበሰበችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፤ መሪያችንም መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እኛን የሰበሰበችበት፤ አምላካዊ ሰማያዊና ዘለዓለማዊ ዓላማ እንዳላት የምንዘነጋው አይደለም፡፡
የቤተ ክርስቲያናችን ዓላማ ወንጌለ መንግሥተ ሰማያትን ማስተማርና መንፈሳዊ አገልግሎትን ለእግዚአብሔርና ለሕዝበ ክርስቲያኑ ማበርከት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ሳይዛባ፣ ሳይፋለስ፣ ፈሩን ሳይለቅ በነበረበት ለማስቀጠል የመንበረ ሐዋርያት ወራሾች ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዓመት ሁለት ጊዜ በቋሚነት እየተሰበሰቡ፣ ስለአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ እየገመገሙ፣ እየመከሩና እየወሰኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እምነትዋንና ሥርዓቷን እንዲጠብቁ ቅዱሳን አበው በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ደንግገዋል፡፡ የዛሬው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤም ይህንን ቀኖና ተከትሎ የሚካሄድ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነትዋን፣ (ዶግማዋን) ቀኖናዋን፣ ታሪኳን ጠብቃ የቆየች ጥንታዊት የሃይማኖት ተቋም መሆንዋ በዓለም ታሪክ የተደገፈ ሐቅ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንዋ አስተዳደር ሂደት ሲመረመር ግን እጅግ የተንዛዛ ቢሮክራሲ የሰፈነበትና የሰው ኀይል አመዳደቡም ከመሠረታዊው ተልእኮ ዕቅድ ጋር ያልተቀናጀ ከመሆኑም በላይ የሠራተኛው አቀጣጠር የሥራ ችሎታን፣ ዕውቀትንና ልምድን እንደ መስፈርት ወስዶ የተፈጸመ ባለመሆኑ የሠራተኛው ቊጥር ከሚያስፈልገው በላይ ወጥቶ ይታያል፤ ወደ ውስጥ ገባ ብሎ ሲመረመርም በወገንተኝነትና በሙስና የተቀጠረ መሆኑንና እንዲሁም አፈጻጸሙ የተለያዩ የሥነ ምግባር ብልሹነት በስፋት የሚያንጸባርቅ ሆኖ ይስተዋላል፡፡
ይህ ከቤተ ክርስቲያኒቷ ክብርና ቅድስና ጋር የማይጣጣም ሂደት በመሆኑ ሁኔታውን ለማረም ቅዱስ ሲኖዶሱ አስቸኳይ እርምጃ ሊወስድበት ይገባል፡፡ አስፈላጊው እርማት በወቅቱ ሳይደረግ በመቅረቱ፣ የምእመናኑ በቤተ ክርስቲያኒቷ አመራር ላይ ቅሬታና እምነት ማጣትን እያሳደረ ሁኔታውም እየተባባሰ ሲሄድ ይታያል፡፡ ስለዚህ ታሪክ እንዳይፈርድብን ካህናቱንና ምእመናኑን በማስተባበር አስቸኳይ የእርምት እርምጃ መውሰድ እጅግ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ የሀገሪቱ መንግሥት ሙስናን ለማጥፋት በሚታገልበት ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሙስና በፍጹም መታየት የለበትም፡፡
የቤተ ክርስቲያናችንን ስም ለመጠበቅና ክብርዋን ለማደስ እንዲቻል የሚከተሉት ሥር ነቀል የለውጥ እርምጃዎች በቈራጥነት ተግባራዊ እንዲሆኑ ለማሳሰብ እወዳለሁ፡፡
1.ብልሹ አሠራርን ለማረምና ለማስወገድ፤
ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ እንዲሁም ከምእመናን የተውጣጡ አባላት የሚገኙበት ‹‹የፀረ ሙስና ዐቢይ ኮሚቴ›› እንዲቋቋም ሆኖ ፍትሓዊ በሆነ መንገድ ሁኔታውን እየመረመረ ስንዴውን ከእንክርዳድ ለይቶ እንዲያቀርብ ማድረግና እንክርዳድ ሆኖው በሚገኙት ላይ አስተማሪ የሚሆን ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ፡፡
2. አስተዳደሩን በአዲስ መልክ ስለማዋቀር፤
የቤተ ክርስቲያኒቱን የአስተዳደር መዋቅርና የሚሠሩባቸውን ደንቦችና ሕጎች ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን ጨምሮ የሚመረምርና የማሻሻያ ሐሳብ የሚያቀርብ ‹‹የአስተዳደር መሻሻል ዐቢይ ኮሚቴ›› እንዲቋቋምና፤ አባላቱም አሁንም ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከካህናትና ከምእመናን የተውጣጡ እንዲሆኑ ተደርጎ አስተዳደሩ ለለውጥ የተዘጋጀ ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲኖረው ለማድረግና ውጤት ተኮር የሆነ ሥርዐት ለመዘርጋት የሚያስችል የማሻሻያ ጥናታዊ ሐሳብ እንዲያቀርብ ማድረግ፤ በተጨማሪም አስተዳደሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን ራእይና ተልእኮ በግልጽ የሚያሳይ እስትራቴጂካዊ የአመራር ሥርዐት እንዲነድፍና የተሟላ የማሻሻያ ሐሳብ እንዲያቀርብ ማድረግ፡፡
3. የፋይናንስ አያያዝን በተመለከተ፤
የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብ አያያዝና አጠቃቀም ሥርዐት ዘመናዊ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት ባለው መልኩ ለማደራጀት የሚያስችል ሥርዐት እንዲዘረጋ ለማድረግ ጥናት እንዲያቀርብ ባለሙያዎች በአባልነት የሚገኙበት ‹‹የገንዘብ አያያዝ ሥርዐት ማሻሻያ ዐቢይ ኮሚቴ›› እንዲቋቋምና ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ድረስ የሚሠራበትን ሥርዐት መርምሮ አንድ ወጥ የሆነ ሥርዐት ለመዘርጋት የሚያስችል ሐሳብ እንዲቀርብ ማድረግ፡፡
እነዚህ ሦስት መሠረታዊ እርምጃዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ጤናማ ሂደት የሚወስኑ እጅግ አስፈላጊ የሆኑ እርምጃዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ የቀረበው ሐሳብ በአስቸኳይ ተግባራዊ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ቈራጥ የሆነ ውሳኔ ሊሰጥበት ይገባል፡፡ ሥር ሰዶ የሚታየው አሳፋሪና አሳዛኝ ብልሹ አሠራር ሳይታረም ቢቀጥል ቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ችግር ውስጥ እንደምትወድቅ በግልጽ እየታየ ነው፡፡ እኛ በአመራር ላይ ያለነውን ሰዎች ይህ ብልሹ አስተዳደር እንደሚያስወቅሠንና እንደሚያስፈርድብን ልንገነዘብ ይገባል፡፡ እርምጃው፣ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ቈራጥነትን ይጠይቃል፡፡ በአጭር ጊዜ የተፈለገውን ለውጥ ለማምጣት የሚያዳግት ቢሆንም የለውጡን መሠረት ግን በአስቸኳይ ማስቀመጥና አቅጣጫውን መቀየስ እጅግ አስፈላጊ መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤
ይህንን ስንል ግለሰቦችን ለማደንና ለመጒዳት አይደለም፤ የምናተኵረው ወደ ሥርዐቱ እንጂ ወደ ግለሰቦች አይደለም፡፡ ፀረ ሙስና ሥርዐት ከተደነገገ ሙስናው ይጠፋል፤ ቤተ ክርስቲያን ሕይወት ታገኛለች፤ ዓላማችን ይህ ብቻ ነው፤ ሌላ ጒዳይ የለንም፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን በተመለከተ፤
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአራት ሊቃነ ጳጳሳትና በአራት ሥራ አስኪያጆች እንዲተዳደር የተወሰነ ቢሆንም፣ አሁን እየተሠራ ያለው በሁለት ሊቃነ ጳጳሳትና በአራት ሥራ አስኪያጆች ነው፡፡ ይሁን እንጂ እንደታሰበው አደረጃጀቱ ችግር ፈች ሆኖ አልተገኘም፡፡ በዋነኛነት ምደባው ጥናት ተደርጎለትና መስፈርት ወጥቶለት በውድድር መሆን ሲገባው ይህ ባለመፈጸሙ እንዲሁም በወረዳ ደረጃ ላለው መዋቅር ሥልጣን ተከፍሎ ያልተሰጠውና ሥራውን የማይሠራ ስለሆነ ችግሩ እየገዘፈና እየተመሰቃቀለ በመምጣቱ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መንሥኤ በመሆኑ አሁን ያለውን አደረጃጀት መቀየር አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡
ስለዚህ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቅዱስ ፓትርያርኩ ሀገረ ስብከት ስለሆነ፤ በአስተዳደር ችሎታው ጠንካራ የሆነ ረዳት ሊቀ ጳጳስ በመመደብ፤ እንዲሁም እርሱን የሚረዱ በሥራ ችሎታው ብቁና ጠንካራ የሆኑ ሥራ አስኪያጆችን መድቦ በመሰየም ተጠያቂነትና ኀላፊነት ያለው ግልጽ የሆነ ጠንካራ የአስተዳደር ሥርዐት መዘርጋት ያስፈልጋል፡፡
እግዚአብሔር በልዩ አጠራሩ ሁላችንንም ጠርቶና መርጦ እዚህ ቦታ አስቀምጦናል፤ በዚህ ቦታ ሆነን የምናካሂደው ጉባኤና የምናሳልፈው ውሳኔ ሁሉ በእግዚአብሔር፣ በታሪክና በመጪው ትውልድ ፊት ሁልጊዜ በሚዛን እየተመዘነ የሚኖር እንደሆነ ልንዘነጋው አይገባም፡፡
እኔም ሆንሁ ብፁዓን አባቶች ሁላችሁም፤ ትናንት አንድ ላይ ሆነን በቤተ ክርስቲያናችን መታየት የሚገባቸውን የአሠራር ክፍተቶች አሉና መፍትሄ እናበጅላቸው ብለን በዚህ ቦታ ብዙ ጊዜ አንሥተናል፡፡ ይሁን እንጂ እስከአሁን አልተስተካከሉም፤ በመሆኑም፤ እነርሱን ዛሬ በፍጥነት ማስተካከል ካልቻልን በቅድሚያ በእኛ ላይ የሚፈርድ የገዛ ራሳችን ኅሊና ነው፤ በይቀጥላልም እግዚአብሔርም ሌላውም ሁሉ ይፈርድብናል፡፡
እኔ ወንድማችሁንም በዚህች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዳገለግልና እንድላላክ መርጣችሁ በዚህ ትልቅ ኀላፊነት ወንበር ላይ ስታስቀምጡኝ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ የምእመናንን የልብ ትርታ እያዳመጥሁ ለእናንተ ለብፁዓን አባቶች ሳቀርብ ይሁንታውንና እገዛውን እየለገሳችሁኝ የጋራ ኀላፊነታችንን እንድንወጣ መሆን አለበት፡፡
ስለሆነም ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች የሚቀርፍ አጀንዳ በመያዝ፣ በማጽደቅ፣ በስፋትና በጥልቀት በመወያየት ቤተ ክርስቲያናችንን የሚታደግ ችግሮችን የሚቀርፍ መመሪያ እንዲያወጣ ጥሪዬን በእግዚአብሔር ስም አስተላልፋለሁ፡፡
እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!