• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ግንቦት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

May 29, 2013

ቅዱስነታቸው ከተሾሙ በኋላ የመጀሪያው የርክበ ካህናት ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዐት ላይ የሚከተለውን ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ምስጋና የባሕርዩ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ሁላችንንም ከየሀገረ ስብከቱ አሰባስቦ በዚህ ሐዋርያዊ፣ ቀኖናዊና ዐቢይ ጉባኤ ተገናኝተን ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ለመወያየት ስለፈቀደ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡ እንደዚሁም በዚህ ዐቢይ ጉባኤ ለመገኘት ከቅርብም ከሩቁም የመጣችሁ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሁላችሁም እንኳን በደኅና መጣችሁ፡፡

‹‹አስተጋብአተነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ሐዋርያት፤ ኀበ ሀለዉ አግብርተ እግዚአብሔር – ሐዋርያት የሰበሰቧት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር አገልጋዮች ወደአሉበት ሰበሰበችን› (ቅዱስ ያሬድ)፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው እዚህ ቅዱስ ስፍራ የሰበሰበችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፤ መሪያችንም መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እኛን የሰበሰበችበት፤ አምላካዊ ሰማያዊና ዘለዓለማዊ ዓላማ እንዳላት የምንዘነጋው አይደለም፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን ዓላማ ወንጌለ መንግሥተ ሰማያትን ማስተማርና መንፈሳዊ አገልግሎትን ለእግዚአብሔርና ለሕዝበ ክርስቲያኑ ማበርከት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ተልእኮ ሳይዛባ፣ ሳይፋለስ፣ ፈሩን ሳይለቅ በነበረበት ለማስቀጠል የመንበረ ሐዋርያት ወራሾች ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዓመት ሁለት ጊዜ በቋሚነት እየተሰበሰቡ፣ ስለአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ እየገመገሙ፣ እየመከሩና እየወሰኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እምነትዋንና ሥርዓቷን እንዲጠብቁ ቅዱሳን አበው በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ደንግገዋል፡፡ የዛሬው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤም ይህንን ቀኖና ተከትሎ የሚካሄድ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነትዋን፣ (ዶግማዋን) ቀኖናዋን፣ ታሪኳን ጠብቃ የቆየች ጥንታዊት የሃይማኖት ተቋም መሆንዋ በዓለም ታሪክ የተደገፈ ሐቅ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንዋ አስተዳደር ሂደት ሲመረመር ግን እጅግ የተንዛዛ ቢሮክራሲ የሰፈነበትና የሰው ኀይል አመዳደቡም ከመሠረታዊው ተልእኮ ዕቅድ ጋር ያልተቀናጀ ከመሆኑም በላይ የሠራተኛው አቀጣጠር የሥራ ችሎታን፣ ዕውቀትንና ልምድን እንደ መስፈርት ወስዶ የተፈጸመ ባለመሆኑ የሠራተኛው ቊጥር ከሚያስፈልገው በላይ ወጥቶ ይታያል፤ ወደ ውስጥ ገባ ብሎ ሲመረመርም በወገንተኝነትና በሙስና የተቀጠረ መሆኑንና እንዲሁም አፈጻጸሙ የተለያዩ የሥነ ምግባር ብልሹነት በስፋት የሚያንጸባርቅ ሆኖ ይስተዋላል፡፡

ይህ ከቤተ ክርስቲያኒቷ ክብርና ቅድስና ጋር የማይጣጣም ሂደት በመሆኑ ሁኔታውን ለማረም ቅዱስ ሲኖዶሱ አስቸኳይ እርምጃ ሊወስድበት ይገባል፡፡ አስፈላጊው እርማት በወቅቱ ሳይደረግ በመቅረቱ፣ የምእመናኑ በቤተ ክርስቲያኒቷ አመራር ላይ ቅሬታና እምነት ማጣትን እያሳደረ ሁኔታውም እየተባባሰ ሲሄድ ይታያል፡፡ ስለዚህ ታሪክ እንዳይፈርድብን ካህናቱንና ምእመናኑን በማስተባበር አስቸኳይ የእርምት እርምጃ መውሰድ እጅግ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ የሀገሪቱ መንግሥት ሙስናን ለማጥፋት በሚታገልበት ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሙስና በፍጹም መታየት የለበትም፡፡

የቤተ ክርስቲያናችንን ስም ለመጠበቅና ክብርዋን ለማደስ እንዲቻል የሚከተሉት ሥር ነቀል የለውጥ እርምጃዎች በቈራጥነት ተግባራዊ እንዲሆኑ ለማሳሰብ እወዳለሁ፡፡

1.ብልሹ አሠራርን ለማረምና ለማስወገድ፤
ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ እንዲሁም ከምእመናን የተውጣጡ አባላት የሚገኙበት ‹‹የፀረ ሙስና ዐቢይ ኮሚቴ›› እንዲቋቋም ሆኖ ፍትሓዊ በሆነ መንገድ ሁኔታውን እየመረመረ ስንዴውን ከእንክርዳድ ለይቶ እንዲያቀርብ ማድረግና እንክርዳድ ሆኖው በሚገኙት ላይ አስተማሪ የሚሆን ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ፡፡

2. አስተዳደሩን በአዲስ መልክ ስለማዋቀር፤
የቤተ ክርስቲያኒቱን የአስተዳደር መዋቅርና የሚሠሩባቸውን ደንቦችና ሕጎች ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን ጨምሮ የሚመረምርና የማሻሻያ ሐሳብ የሚያቀርብ ‹‹የአስተዳደር መሻሻል ዐቢይ ኮሚቴ›› እንዲቋቋምና፤ አባላቱም አሁንም ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከካህናትና ከምእመናን የተውጣጡ እንዲሆኑ ተደርጎ አስተዳደሩ ለለውጥ የተዘጋጀ ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲኖረው ለማድረግና ውጤት ተኮር የሆነ ሥርዐት ለመዘርጋት የሚያስችል የማሻሻያ ጥናታዊ ሐሳብ እንዲያቀርብ ማድረግ፤ በተጨማሪም አስተዳደሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን ራእይና ተልእኮ በግልጽ የሚያሳይ እስትራቴጂካዊ የአመራር ሥርዐት እንዲነድፍና የተሟላ የማሻሻያ ሐሳብ እንዲያቀርብ ማድረግ፡፡

3. የፋይናንስ አያያዝን በተመለከተ፤
የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብ አያያዝና አጠቃቀም ሥርዐት ዘመናዊ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት ባለው መልኩ ለማደራጀት የሚያስችል ሥርዐት እንዲዘረጋ ለማድረግ ጥናት እንዲያቀርብ ባለሙያዎች በአባልነት የሚገኙበት ‹‹የገንዘብ አያያዝ ሥርዐት ማሻሻያ ዐቢይ ኮሚቴ›› እንዲቋቋምና ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ድረስ የሚሠራበትን ሥርዐት መርምሮ አንድ ወጥ የሆነ ሥርዐት ለመዘርጋት የሚያስችል ሐሳብ እንዲቀርብ ማድረግ፡፡

እነዚህ ሦስት መሠረታዊ እርምጃዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ጤናማ ሂደት የሚወስኑ እጅግ አስፈላጊ የሆኑ እርምጃዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ የቀረበው ሐሳብ በአስቸኳይ ተግባራዊ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ቈራጥ የሆነ ውሳኔ ሊሰጥበት ይገባል፡፡ ሥር ሰዶ የሚታየው አሳፋሪና አሳዛኝ ብልሹ አሠራር ሳይታረም ቢቀጥል ቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ችግር ውስጥ እንደምትወድቅ በግልጽ እየታየ ነው፡፡ እኛ በአመራር ላይ ያለነውን ሰዎች ይህ ብልሹ አስተዳደር እንደሚያስወቅሠንና እንደሚያስፈርድብን ልንገነዘብ ይገባል፡፡ እርምጃው፣ ሥር ነቀል ለውጥ ለማምጣት ቈራጥነትን ይጠይቃል፡፡ በአጭር ጊዜ የተፈለገውን ለውጥ ለማምጣት የሚያዳግት ቢሆንም የለውጡን መሠረት ግን በአስቸኳይ ማስቀመጥና አቅጣጫውን መቀየስ እጅግ አስፈላጊ መሆኑ ሊሠመርበት ይገባል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

ይህንን ስንል ግለሰቦችን ለማደንና ለመጒዳት አይደለም፤ የምናተኵረው ወደ ሥርዐቱ እንጂ ወደ ግለሰቦች አይደለም፡፡ ፀረ ሙስና ሥርዐት ከተደነገገ ሙስናው ይጠፋል፤ ቤተ ክርስቲያን ሕይወት ታገኛለች፤ ዓላማችን ይህ ብቻ ነው፤ ሌላ ጒዳይ የለንም፡፡

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን በተመለከተ፤

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአራት ሊቃነ ጳጳሳትና በአራት ሥራ አስኪያጆች እንዲተዳደር የተወሰነ ቢሆንም፣ አሁን እየተሠራ ያለው በሁለት ሊቃነ ጳጳሳትና በአራት ሥራ አስኪያጆች ነው፡፡ ይሁን እንጂ እንደታሰበው አደረጃጀቱ ችግር ፈች ሆኖ አልተገኘም፡፡ በዋነኛነት ምደባው ጥናት ተደርጎለትና መስፈርት ወጥቶለት በውድድር መሆን ሲገባው ይህ ባለመፈጸሙ እንዲሁም በወረዳ ደረጃ ላለው መዋቅር ሥልጣን ተከፍሎ ያልተሰጠውና ሥራውን የማይሠራ ስለሆነ ችግሩ እየገዘፈና እየተመሰቃቀለ በመምጣቱ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መንሥኤ በመሆኑ አሁን ያለውን አደረጃጀት መቀየር አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡

ስለዚህ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቅዱስ ፓትርያርኩ ሀገረ ስብከት ስለሆነ፤ በአስተዳደር ችሎታው ጠንካራ የሆነ ረዳት ሊቀ ጳጳስ በመመደብ፤ እንዲሁም እርሱን የሚረዱ በሥራ ችሎታው ብቁና ጠንካራ የሆኑ ሥራ አስኪያጆችን መድቦ በመሰየም ተጠያቂነትና ኀላፊነት ያለው ግልጽ የሆነ ጠንካራ የአስተዳደር ሥርዐት መዘርጋት ያስፈልጋል፡፡

እግዚአብሔር በልዩ አጠራሩ ሁላችንንም ጠርቶና መርጦ እዚህ ቦታ አስቀምጦናል፤ በዚህ ቦታ ሆነን የምናካሂደው ጉባኤና የምናሳልፈው ውሳኔ ሁሉ በእግዚአብሔር፣ በታሪክና በመጪው ትውልድ ፊት ሁልጊዜ በሚዛን እየተመዘነ የሚኖር እንደሆነ ልንዘነጋው አይገባም፡፡

እኔም ሆንሁ ብፁዓን አባቶች ሁላችሁም፤ ትናንት አንድ ላይ ሆነን በቤተ ክርስቲያናችን መታየት የሚገባቸውን የአሠራር ክፍተቶች አሉና መፍትሄ እናበጅላቸው ብለን በዚህ ቦታ ብዙ ጊዜ አንሥተናል፡፡ ይሁን እንጂ እስከአሁን አልተስተካከሉም፤ በመሆኑም፤ እነርሱን ዛሬ በፍጥነት ማስተካከል ካልቻልን በቅድሚያ በእኛ ላይ የሚፈርድ የገዛ ራሳችን ኅሊና ነው፤ በይቀጥላልም እግዚአብሔርም ሌላውም ሁሉ ይፈርድብናል፡፡

እኔ ወንድማችሁንም በዚህች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዳገለግልና እንድላላክ መርጣችሁ በዚህ ትልቅ ኀላፊነት ወንበር ላይ ስታስቀምጡኝ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ የምእመናንን የልብ ትርታ እያዳመጥሁ ለእናንተ ለብፁዓን አባቶች ሳቀርብ ይሁንታውንና እገዛውን እየለገሳችሁኝ የጋራ ኀላፊነታችንን እንድንወጣ መሆን አለበት፡፡

ስለሆነም ከላይ የተጠቀሱትን ችግሮች የሚቀርፍ አጀንዳ በመያዝ፣ በማጽደቅ፣ በስፋትና በጥልቀት በመወያየት ቤተ ክርስቲያናችንን የሚታደግ ችግሮችን የሚቀርፍ መመሪያ እንዲያወጣ ጥሪዬን በእግዚአብሔር ስም አስተላልፋለሁ፡፡

እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc2013-05-29 17:13:002024-12-03 20:31:40ግንቦት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ሚያዝያ 27 ቀን 2005 ዓ.ም የበዓለ ትንሣኤ ሐዋርያዊ መልእክት Link to: ሚያዝያ 27 ቀን 2005 ዓ.ም የበዓለ ትንሣኤ ሐዋርያዊ መልእክት ሚያዝያ 27 ቀን 2005 ዓ.ም የበዓለ ትንሣኤ ሐዋርያዊ... Link to: ከግንቦት 21-30 ቀን 2005 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች Link to: ከግንቦት 21-30 ቀን 2005 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች ከግንቦት 21-30 ቀን 2005 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top