መስከረም 16 ቀን 2013 ዓ.ም.የመስቀል ደመራ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በአጠቃላይ በዚህ የመስቀል አደባባይ የተገኛችሁና በየአካባቢው ሆናችሁ በዓለ መስቀሉን እያከበራችሁ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፤

በኀይለ መስቀሉ ሕዝቡንና አሕዛቡን አንድ አድርጎ በወንጌለ ሰላሙ ወደ እርሱ ያቀረበን እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለበዓለ መስቀሉ አደረሳችሁ።!
‹‹መስቀል በሉ፤ ኪያሁ ተወከሉ፤
መስቀል እያላችሁ ተናገሩ፤ እሱንም ተማመኑ።››
(ቅዱስ ያሬድ)
መስቀል እንደየፅንሰ ሐሳቡ ወይም እንደየዐውደ ንባቡ የተለያየ ትርጒም አለው፤ ይሁን እንጂ ሲጠቃለል ትእምርት፤ ተጋድሎና መሥዋዕትነት በሚሉ ሦስት መሠረተ ሓሳቦች ሊጠቃለል ይችላል፡፡ ሦስቱ መሠረተ ሓሳቦች ሲገናዘቡ ደግሞ ወደ አንድ ነገረ አመሥጥሮ ይመጣሉ ፡፡ ትእምርተ መስቀል እያልን የምንገልጽው አገላለጽ በዐይናችን የምናየውን፣ በአንገታችን የምናስረውን፣ በልብሳችንና በአካላችን የምንቀርፀውን፣ በእጃችን የምንጨብጠውን፣ በአፋችን የምንሳለመውና ከቊስ የተሠራውን መስቀልን ማመልከታችን ነው፤ ይህን ትእምርተ መስቀል ባየን ቊጥር ክርስቶስ የኀጢአታችንን ዕዳ ለመክፈል የተቀበለውን ጸዋትወ መከራ እናስባለን፤ ድኅነታችንም ክርስቶስ በመስቀል ተሰቅሎ ባደረገው መሥዋዕታዊ ቤዛነት እንደተፈጸመ እናስታውሳለን፤ በዚህም እግዚአብሔር ለኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅር እንገነዘባለን ፡፡
እኛ ክርስቲያኖች በትእምርተ መስቀሉ አማካኝነት ድኅነተ ዓለምን እንሰብካለን፤ ትእምርተ መስቀሉ በሃይማኖት እንባረክበታለን፤ እንባርክበታለንም፤ ትእምርተ መስቀሉ የክርስቶስን መከራና አዳኝነት የወከለ መንፈሳዊ ትእምርት በመሆኑ እናከብረዋለን፤ በቤተ ክርስቲያን ጕልላትም ሆነ በአካላችን ሁሉ ትእምርቱን በማሳየት ነገረ ድኅነትን ለዓለም እናስተምርበታለን፡፡
ሁለተኛው የመስቀል ትርጒም ተጋድሎ ነው፤ ዓለም የዳነበት ነገረ መስቀሉን በማመን፣ አዳኙን ኢየሱስ ክርስቶስን በመከተልና በማምለክ ወደ እግዚአብሔር በሚቀርቡ ክርስቲያኖች ላይ ክፉው መንፈስ ምን ጊዜም መከራ ማምጣቱን አያቆምም፤ ታድያ በክፉው መንፈስ አዝማችነት በክርስቲያኖች ላይ የሚዘንበውን መከራ ሳይፈሩ፣ ሳይሰቀቁና ከእምነታቸው ዝንፍ ሳይሉ በጽንዐ ሃይማኖት የሚቀበሉት መከራና ተጋድሎ መስቀል ይባላል፤ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹መስቀሌን ተሸክሞ ሊከተለኝ የማይወድ የኔ ሊሆን አይችልም›› ያለው ይህ ዐይነቱን ተጋድሎ ሲያመለክት እንደሆነ ግልጽ ነው ፡፡ ይህንን ክርስቶሳዊ አስተምህሮ ተከትለው በዓለማችን ስፍር ቊጥር የሌላቸው ሰማዕታት መስቀላዊ ተጋድሎን በመሸከምና ሕይወታቸውን ገብረዋል፤ አሁንም እየገበሩ ነው፡፡
ሦስተኛውና እጅግ በጣም ጥልቅ የሆነው የመስቀል ትርጒም ደግሞ መሥዋዕታዊ ቤዛነት ነው፤ በዚህ ዐውደ ምንባብ መሥዋዕት ማለት ለሌላው ወገን ሲባል የሚከፈል ኅልፈተ ሕይወት ነው፤ ቤዛነት ሲባልም በመያዣነት የተያዘን ነገር ለማስለቀቅ የሚከፈል ዋጋ ነው፤ ከዚህ አንጻር መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጠቃላይ ለትዝምደ ሰብእ ሲል በመስቀል ላይ ሕይወቱን አሳልፎ በመስጠት ሠውቶአል፤ በኀጢአትና በፍዳ ምክንያት በዲያብሎስ እጅ ተይዘው የነበሩትን ነፍሳተ ሰብእንም ደሙን ቤዛ አድርጎ ለአባቱ በማቅረብ ከኀጢአትና ኀጢአት ካመጣው ፍዳ ነፃ አድርጎአል፤ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹አኮ በዘይማስን ብሩር ወወርቅ ዘተቤዘወክሙ እምውስተ ዘኢይበቊዕ ምግባሪክሙ ዘተመጠውክሙ እምአበዊክሙ አላ በክቡር ደሙ ለክርስቶስ፣ ካባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከማይጠቅም ሥራችሁ ቤዛ የሆናችሁ በሚጠፋ ብርና ወርቅ አይደለም፤ በከበረ የክርስቶስ ደም እንጂ›› ያለው ይህንን መሥዋዕታዊ ቤዛነት ለማመልከት ነው ፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ክቡራንና ክቡራት የበዓሉ ተሳታፊዎች፤

ዲያብሎስ ቀድሞውኑም የሰዎችን ነፍሳት በእጁ ሊያስገባ የቻለው በኀጢአትና ኀጢአት ባስከተለው ፍዳ ምክንያት ነበረ፤ ሰዎች በደመ ክርስቶስ ቤዛነት ከኀጢአትና ከፍዳው ነፃ ሲሆኑ በዲያብሎስ እጅ የሚያዙበት ምክንያት አልነበረምና ከዲያብሎስ የግዞት ከተማ ወጥተው ወደ ክርስቶስ ከተማ ወደ መንግሥተ ሰማያት ገብተዋል፤ ይህም ድርጊት በመስቀል ላይ የተፈጸመና መስቀል ያስገኘው ድል ስለሆነ መስቀል ይባላል፤ በሌላ በኩል መስቀል የሚለው ቃል ምሥጢሩን ተከትሎ ወደ አማርኛ ሲተረጐም ‹‹መሰቀል›› ይባላል፤ ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች በጻፈው መልእክት ‹‹ወአንሰ ሐሰ ሊተ ኢይዜኀር ዘእንበለ በመስቀሉ ለኢየሱስ ክርስቶስ እግዚእነ፤ እኔስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ካልሆነ በቀር በሌላ አልመካም›› ሲል የገለጸው መስቀሉን መሥዋዕታዊ ቤዛነት ብሎ በማመሥጠር ነው፤ የሚያድን፣ የሚያስታርቅ፣ ሰላምንና አንድነትን የሚያስገኝ፣ ወደ እግዚአብሔር የሚያቀርብ ይህ በኢየሱስ ክርስቶስ የተፈጸመው መሥዋዕታዊ ቤዛነት ነውና፤ ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ቤዛነት ካልሆነ በቀር በሌላ መመካት ጭራሽ የማያስኬድና የማያዋጣ እንደሆነ ነግሮናል፤ እኛም መስቀል ኀይላችን ነው፤ መስቀል ጽናታችን ነው፤ መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው ስንል መሥዋዕታዊ ቤዛነቱን ማመልከታችን እንደሆነ ይታወቃል ፡፡ የመስቀል ትርጒም እንደየዐውደ ምንባቡ በሦስት ዋና ዋና ትርጉሞች ቢነገርም የሦስቱም መዳረሻ ምሥጢር መዳንን ማመልከት ነው፤ ትእምርተ መስቀሉን ዐርማችን አድርገን የምንይዘው የምንሳለመውና የምንባረክበት ለመዳን ነው፤ ስለሃይማኖታችን ስንል የምንቀበለው መስቀላዊ ተጋድሎና መከራም ለመዳን ነው፤ በጌታችን የተፈጸመልን መሥዋዕታዊ ቤዛነትም እኛን ለማዳን ነው፤ ስለሆነም በሁሉም አቅጣጫ የነገረ መስቀሉ መነሻ መገሥገሻና መድረሻ መዳንና መዳን ብቻ ሆኖ እናገኘዋለን፤ ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ ቅዱስ ያሬድም ‹‹መስቀል በሉ፤ እሱንም ተማመኑ›› ብሎ የዘመረው ከፍ ብሎ እንደተገለጸው በቤዛነት ደረጃ በመስቀል ላይ ከሆነው የክርስቶስ መሥዋዕታዊ ቤዛነት በቀር ሌላ መዳኛ እንደሌለ ለመግለጽ ነው፤ በሥጋም በነፍስም፣ በሰማይም በምድርም የቤዛነትን ተግባር ፈጽሞ ያዳነን ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና መስቀል አዳነን ስንል ክርስቶስ አዳነን ማለት እንደሆነ ልብ ይሏል ፡፡ ይህ ቤዛነት ሰማይንና ምድርን አንድ አድርጎ አስታርቆአል፤ ይቅርታም አጎናጽፎአል፤ ሰላምንም አስፍኖአል፤ ትዝምደ ሰብእን በአጠቃላይ ወደ አንድነት አምጥቶአል ፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራንና ክቡራት የበዓሉ ተሳታፊዎች፤

መስከረም 17 ቀን በየዓመቱ የምናከብረው የመስቀል በዓል ትእምርተ መስቀሉ ከተቀበረበት ጕድጓድ በአምላካዊ ተኣምር ስለተገኘ ብቻ ሳይሆን ከዚያ ባለፈ ለዘለዓለሙ ሲያበራ የሚኖር አምላካዊ የማዳን ኀይልንም ለመመስከር ነው፤ ይህ የማይደበዝዝ ብርሃን በትክክል በሕይወታችን ውስጥ ከበራ ሰላምን እናገኛለን፤ አንድነታችንን እናጸናለን፤ ሁሉንም ነገር በዕርቅና በይቅርታ እናልፈዋለን፤ ዐይናችን ልባችንና ኅሊናችን ወደ ልማትና ሰውን ሊጠቅም ወደሚችል ተግባር እንጂ በሰው ላይ ጥፋትን ወደሚያስከትል ነገር አያተኵርም ፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያ ይህንን የመሰለ ምሥጢረ አምላክ የተሸከመ መስቀልን በግንባርዋ ቀርጻ በትከሻዋ ተሸክማ በሃይማኖቱ ከብራ ባለችበት ሁኔታ ዛሬ የምናየው የመስቀል ተቃራኒ ድርጊት ከምን የመጣ ነው? በመስቀላዊቷ ሀገር በኢትዮጵያ መጨካከንን፣ መገዳደልን፣ መለያየትን፣ መነቃቀፍን፣ ያስተማረና ያስለመደብን ከቶ ማን ይሆን? እውን አሁን የምናየውና የምንመለከተው ሁሉ የኢትጵያውያን ጠባይ ነውን? በፍጹም አይደለም፤ ይህ እየሆነ ያለው የሀገራችንን አንድነት፣ ልማትና እድገት እንደ እሬት ከሚመራቸው የውጭ ኀይሎች የሚሰነዘር እንጂ ከኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን አይደለም፤ ሰፊው አስተዋይ ሕዝብ ከነባሩ ኢትዮጵያዊ ቅዱስ ዕሴትና ትውፊት፣ ባህልና ማኅበራዊ ኑሮ ያልተለየ አስተዋይ ሕዝብ ነው፤ ኢትዮጵያዊ አብሮ መብላትን፣ አብሮ መኖርን፣ ተደጋግፎና ተጋግዞ የችግር ዘመን ማሳለፍን ያካበተ ቅዱስ ሕዝብ ሆኖ ለሺሕዎች ዘመናት ኖሮአል፤ ለማንነቱ መገለጫ ከዚህ የበለጠ ማስረጃ የለም፤ ታድያ ይህንን የራሳችን ነባርና ቅዱስ ባህልን ትተን የሌሎቹን ደባል ባህል ለምን አስፈለገን? ደባሉ ባህልስ ከጥፋትና ከውድመት በቀር ምን አስገኘልን?
እውነቱን ለመናገር ኢትዮጵያዊውን ባህል አቃልለን ሀገሪቱን ወደማያስፈልግ አቅጣጫ እየነዳናት ያለን ፊደል ቈጠርን፣ ተራቀቅን፣ የባሕር ማዶውን ጥበብ ቀሰምን፤ ተመራመርን የምንል ልሂቃን ሰዎች ነን፤ ግን እኮ መስቀሉ ‹‹የናንተ ጥበብ ሞኝነት ነው›› ብሎናል፤ ከመስቀሉ በላይ ለመሆን እየተፈለገ ከሆነ አያዋጣም፤ አያዛልቅምም፣ ሰፊውና ቅዱሱ የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን ጠባዩን አልለወጠም፤ አንድነቱን አልጠላም፤ ሰላሙን ሊነኩበት አይፈልግም፤ በማይበጠስ የባህል፣ የሃይማኖት፣ የማኅበራዊ ኑሮ፣ የፍቅርና የወንድማማችነት ሐብል የታሠረ ነው፤ አሁንም እኛ የምንመክረውና የምናስተምረው ከሁሉ በፊት ሁሉም የፖለቲካ ልኂቃኖቻችን ያለምንም ልዩነት በአንድ አዳራሽ ተገናኝታችሁ በመወያየት ለዚህ ሀገርና ሕዝብ የሚበጅ ነገርን ፍጠሩ፤ ኢትዮጵያ፣ ሰላም፣ እኩልነት፣ አንድነት፣ የሕይወትና የንብረት ዋስትና ይከበሩ የሚሉትን መሠረታዊ ነገሮች የጋራ አድርጋችሁ ያዙልን፣ ሌላውን ለሕዝቡ ዕድል ስጡትና እሱ ይዳኝ፤ የፈለገውን ርእዮተ ዓለም፣ የፈለገውን መንግሥት ራሱ መርጦ ያስቀምጥ፤ ነገሩ ሁሉ በዚህ አልቆ ወደ ልማትና እድገት እንግባ፤ ወጣት ልጆቻችንም እባካችሁ ሰከን በሉ፤ ጥያቄ አትጠይቁ አንልም፤ ግን የሰውን ሕይወትና ንብረት አታጥፉ፤ የሚጠፋው ንብረት የናንተው ነው፤ በወገናችሁ ላይ አትጨክኑ፣ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ወገናችሁ ነው፤ እየተደረገ ያለው ድርጊት ጥፋትን እንጂ ልማትን አያስገኝም ነው የምንለው ፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራንና ክቡራት የበዓሉ ተሳታፊዎች፣ መስቀልን በየዓመቱ የምናከብረው፤ ምሥጢረ ድኅነትን፣ ምሥጢረ ፍቅርን፣ ምሥጢረ ሰላምና አንድነትን፣ ምሥጢረ ዕርቅና ይቅርታን ልናስታውስበትና ልንማማርበት ብሎም የጋራ ጥቅማችንንና ሃይማኖታችንን በአዲስ ዓመት በአዲስ መንፈስ ለመተግበር ቃል ለመግባት እንጂ በልዩ ልዩ ኅብረ ቀለማት አሸብርቀንና ተሸላልመን እዩን እዩን ለማለት አይደለም፤ ይህ በሚገባ መታወቅ አለበት፤ ከእንግዲህ ወዲህ ባለፈው ዓመት የተከሠቱ ስሕተቶች በሙሉ በሚገባ ታርመው አዲሱ ዓመት የውይይት የመግባባትና የመስማማት እንዲሆን ሁላችንም መጣር አለብን፤ የቃላት ዘለፋና ነቀፋ ከሚያለያዩን፣ ከሚያራርቁንና ውስጣችንን ከሚያቈስሉን በቀር የሚያመጡት ፋይዳ የላቸውም፡፡
ስለሆነም ምሁራን፣ ፖለቲከኞች፣ የሚድያ ተቅዋማት እባካችሁ ልዩነትን ከሚያሰፉ አባባሎች ተቈጠቡ፤ ይልቁንም ሁሉም ኢትዮጵያውያን የኛው ናቸውና መድረክ ፈጥረው በጋራ ሆነው ለጋራ ሀገር በመወያየት መፍትሔ እንዲያስገኙ በፍቅርና በክብር መጐትጐት ማበረታታትና ማጠናከር ይኖርብናል፤ ይህንን ስናደርግ ሁላችንም ተጠቃሚዎች እንሆናለን ፡፡
በመጨረሻም፤ በሀገራችን እየተከሠቱ የሚገኙ መሰናክሎችን ለማስተካከል መንግሥት፣ የፖለቲካ ኀይሎችና ሕዝቡም በአጠቃላይ ጥበብን፣ መመካከርን፣ ሰላምንና ትዕግሥትን ማእከል ባደረገ መልኩ ታላቋ ኢትዮጵያን ወደ አስተማማኝ ሰላምና ዘላቂ አንድነት ለማሸጋገር ያላሰለሰ ጥረት እንዲያደርጉ ደግመን ደጋግመን በእግዚአብሔር ስም መንፈሳዊና አባታዊ ጥሪያችንን በአጽንዖት እናስተላልፋለን ፡፡
መልካም በዓለ መስቀል ያድርግልን! ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

መስከረም 1 ቀን 2013 ዓ.ም. የርእሰ ዐውደ ዓመት ቃለ ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
በሕመም ምክንት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤት የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵውያት በሙሉ፤

የዘመናት ፈጣሪ የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ሁለት ሺሕ ዐሥራ ሁለት ዓመተ ምሕረት ወደ ዘመነ ማቴዎስ ሁለት ሺሕ ዐሥራ ሦስት ዓመተ ምሕረት በሰላም አደረሳችሁ።
«ተዘከርኩ ዓመተ ዓለም ወአንበብኩ
ዓመተ ዓለምን አሰብሁ፥ አነበብሁም፤»
(መዝ. 77፥5)

ሁሉም እንደሚገነዘበው ፍጡር የሆነ ሁሉ የዕድሜ ልክ አለው፤ ፍጡር የሆነ ሁሉ መነሻም፥ መገሥገሻም፥ መድረሻም አለው፤ ፍጡር የሆነ ሁሉ ከዚህ ውጭ አይደለም። መነሻም፥ መገሥገሻም፥ መድረሻም የሌለው አንድ ብቻ ነው፤ እሱም እግዚአብሔር ነው። ሌላው ፍጡር ግን መነሻውም፥ መድረሻውም፥ መገስገሻውም እግዚአብሔር ነው።

ስፍር ቍጥር ከሌላቸው ፍጡራን መካከል አንዱ ጊዜ ነው። እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አቈጣጠር ሳድሲት ተብላ ከምትታወቀው የመጨረሻዋ ደቃቅ የጊዜ ስሌት እስከ ዓመተ ዓለም ያለው ሰፊ የቊጥር ስሌት በተለያዩ ምዕዋዳት እየተሽከረከረ እንደሚኖር እንገነዘባለን። ይህ የጊዜ እሽክርክሪት በእግዚአብሔር ሕግና ቊጥጥር ሥር ያለ በመሆኑ ፍጡራን ሊቈጣጠሩት አይችሉም። ይሁን እንጂ ባይቈጣጠሩትም ሊጠቀሙበት ይችላሉ ብቻ ሳይሆን እንዲሠሩበት በእግዚአብሔር ታዘዋል። እግዚአብሔር ፍጥረታትን ሲፈጥር ለፍጡራን ጥቅም እንጂ እንዲሁ ለከንቱ አልፈጠረም። እንደሌላው ሁሉ ጊዜም ሠርተን ልንጠቀምበት እንደተፈጠረ ተግባሩ ራሱ ምስክር ነው። በሰው የሚደርሱ ኪሳራዎች ሁሉ በተለያየ ስልት ሊተኩ ይችላሉ፤ የጊዜ ኪሳራ ግን መተካት አይቻልም። ያለው ብቸኛ አማራጭ ጊዜን ሳናባክን ጥቅም ላይ ማዋል ነው።

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

የእግዚአብሔር ቃል ዓመተ ዓለምን እንድናስብ የሚያስተምረን ያለ ምክንያት አይደለም፤ ሰው በተፈጥሮ ዐዋቂ ሆኖ የተፈጠረ ቢሆንም ከተሞክሮ የሚወስደው ዕውቀት ከፍ ያለ እንደሆነ የሚያከራክር አይደለም። የተግባር ተሞክሮ የሚገኘው ደግሞ ከሚመጣው ዓመት ሳይሆን ካለፉት ዓመታት ነው። ስለሆነም እግዚአብሔር ዓመተ ዓለምን እንድናስብ የሚያዘን ካለፈው ዘመን ተሞክሮ ወስደን ድክመትን በጥንካሬ በመለወጥ በቍጭት ለተሻለ ሥራ እንድንነሣ ለማስቻል ነው። ከዚህ አንጻር ያለፈውን ዓመት ስንመዝነው በሀገራችን ብዙ ምስቅልቅል እንዲከሠት ምክንያቶች ሆነን መገኘታችን ይታያል።

የአማንያን ሀገር እንደሆነች ኮርተን በምንመሰክርላት ኢትዮጵያ አብያተ ሃይማኖት ሲቃጠሉ፥ አማንያን ሲገድሉ፥ ዜጎች በተለያየ ምክንያት አካላዊ፥ ሥነ ልቡናዊና ኢኮኖሚያዊ ጒዳት ሲደርስባቸው በሀገራቸው በሥጋትና በጭንቀት ሲኖሩ ተስተውሎአል። ይህ የተፈጸመው በሌሎች ባዕዳን ሳይሆን ኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸምነው ኢሰብኣዊ ድርጊት በመሆኑ እጅግ የምናፍርበት ሆኖ ተገኝቶአል። በመሆኑም ይህንን ሁናቴ ለማስተካከል ባለፉት ወራት በተነሣው ግርግር የሞት፣ የአካል ጒዳትና የንብረት ውድመት ያጋጠማቸውን ወገኖች ለመርዳትና ለማቋቋም ቤተ ክርስቲያናችን በምታደርገው መጠነ ሰፊ ርብርብ በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ያላችሁ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ለዚህ ለተቀደሰው ዐላማ እጃችሁን በመዘርጋት እንድትተባበሩ ወቅታዊ መልእክታችን ነው ፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

በኢትዮጵያ ርእሰ ዐውደ ዓመት ቀን ቆመን አዲሱን ዓመት አንድ ብለን ስንጀምር ያለፈውን ዓመት ላፍታ ቆም ብለን ማሰብ ይኖርብናል። ቀጥሎም ባለፈው ዓመት የተከሠቱትን ድክመቶች በአዲሱ ዓመት ላንደግማቸው ቊርጥ ውሳኔ አሳልፈን ወደ ሥራ መግባት ይገባናል። በአዲሱ ዓመት አብያተ ሃይማኖት የማይቃጠሉባትና የማይደፈሩባት፥ ዜጎች በወገኖቻቸው የማይሞቱባት፥ የማይፈናቀሉባትና የማይሠጉባት ሀገር ለማረጋገጥ እያንዳንዱ ዜጋ ቃል ኪዳን መግባት አለበት። ይህ እውን ሊሆን የሚችለው አስተማማኝ ሰላም ሲኖር ነው። ይህ ዐይነቱ አስተማማኝ ሰላም ሊረጋገጥ የሚችለው ደግሞ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ስለ ሰላም፥ ስለ ሀገር አንድነት፥ ስለ ዜጎች እኩልነትና ስለጋራ ጥቅም አንድ ላይ ሆነው በጥልቀት በመመካከር በሚፈጥሩት ሀገራዊ መግባባት እንደሆነ ኢትዮጵያውያን ሁሉ መገንዘብ አለባቸው።ስለሆነም ኢትዮጵያውያን ሁሉ በዚሁ ዙሪያ በአዲሱ ዓመት በአጽንዖት እንዲያስቡበት እንመክራለን። የእልክና የበቀል አመለካከት ሀገራችንን ዋጋ እንዳያስከፍላት መጠንቀቅ አለብን።

በመጨረሻም፤ በአዲሱ ዓመት በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭም ለሚገኙት ለመላው ኢትዮጵያውያን የምናስተላልፈው ጽኑዕ መልእክት፦ ግጭት መፍጠር የተሸናፊነት እንጂ የአሸናፊነት ፍኖት አለመሆኑ፥ በአንጻሩ ደግሞ በክብ ጠረጴዛ ተወያይቶ ችግርን መፍታት ትልቁ ድል እንደሆነ ግንዛቤ ተወስዶ በአዲሱ ዓመት ሁሉም ወገኖች ለሰላም መስፈን ዝግጁ እንዲሆኑ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን። አዲሱ ዘመን የሰላም፥ የልማትና የአንድነት ዘመን ያድርግልን።

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤ ይቀድስ።ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን።