• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ጥቅምት 12 ቀን 2013 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

October 22, 2020

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አራተኛው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ሥነ ሥርዐት የተገኛችሁ ሁሉ፤
በማያልቅ ፍቅሩ እየጠበቀ አገልግሎታችንንም እየባረከ ሁሌ በቸርነቱ ከዘመን ወደ ዘመን የሚያሸጋግረን እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለዓመታዊው የጥቅምት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሁላችንንም በሰላም አደረሰን፤ አደረሳችሁ!!

“ብፁዓን ገባርያነ ሰላም እስመ እሙንቱ ውሉደ እግዚአብሔር ይሰመዩ
የሚያስታርቁ ብፁዓን ናቸው፤ እነሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና።”
(ማቴ. 5፥9)

ይህ ትምህርተ ብፅዕና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰላም፣ ስለ አስታራቂዎችና ዋጋቸውን አስመልክቶ ያስተማረው የሕይወት ቃል ነው፤ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው የሰላም ነገር በሰማይም ሆነ በምድር በፈጣሪም ሆነ በፍጡራን ዘንድ ያለው ዋጋ ተመጣጣኝም ሆነ ተወዳዳሪ አይገኝለትም፤ በሰማይና በምድር ሰላም በጠፋ ጊዜ ሰላምን ለማምጣት ሲባል አምላክ ሰው ሆኖአል፤ ዕርቅን ለማስፈን ሲባል አምላክ በሥጋ በመስቀል ተሰቅሏል፤ በዚህም ሰማይንና ምድርን ወደ ልጁ ኅብረት አምጥቶአል፤ ዕርቁንና ሰላሙንም አረጋግጦአል፡፡ እንግዲህ ይህ ከኅሊና በላይ የሆነውን የአምላክ ሥራ ስናስተውል ሰላምና ዕርቅ፣ ስምምነትና አንድነት በአምላክ ዘንድ ያላቸው ዋጋ ምን ያህል ትልቅ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ በሕዝብና በሕዝብ መካከል እንዲሁም በግለሰቦች መካከል የዕርቅ ተግባር እያከናወኑ ሰላምን የሚያወርዱ ሰዎችም ዋጋቸው የእግዚአብሔር ልጅ መሆንን እንደሆነ ተናግሮ የማይከዳው አምላክ ማረጋገጫ ቃሉ ሰጥቶአል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ!ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤
ሰላምና ዕርቅ የእግዚአብሔር ተቀዳሚ ተግባራት ናቸው፤ እነዚህ ተግባራት በየቀኑ መፈጸምና መከናወን ያለባቸው የእርሱ ሉዓላዊት መንግሥት በሆነችው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፤ የመንግሥቱ ተጠሪ ደግሞ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነው፤ ይህ ጉባኤ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሆኖ ስለዕርቅና ሰላም አበክሮ እንዲሠራ “ጠብቅ፣ አሰማራ” ተብሎ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥልጣን የተሰጠው አካል ነው፤ ምክንያቱም በሰዎች መካከል ሰላም ከሌለ ቤተ ክርስቲያንም ተጎጂ ናትና ነው፤ ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ ጠባቂ እንደሌላቸው በጎች በሰላም ዕጦት ሕይታቸውንና ንብረታቸውን ሲያጡ ከማየት የበለጠ የቤተ ክርስቲያን ጥቃት የለምና፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ ከምንም ጊዜ በላይ በጎቹን ለመጠበቅ የሚተጋበት ጊዜ ላይ መሆኑን በውል መገንዘብ ይገባል፤ ቅዱስ ሲኖዶስ የሁሉም በጎች እኩል ጠባቂ ነውና፤ የገለልተኝነትና የማእከላዊነት አቋሙን ጠብቆ የሁሉም ወገን አባትነቱን ሳያዛንፍ ለልጆቹ ዕርቅና ሰላም መረጋገጥ ሁሉንም በአባታዊ ፍቅር እያቀፈ ማስታረቅ በዚህ ዓመት የመጀመሪያ ተግባሩ ማድረግ ይኖርበታል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ!
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
ሁላችንም እንደምናየው በቃልም ይሁን በመሠረተ ሐሳብ ዕርቅንና ሰላምን የሚቃወም ወገን ፈጽሞ የለም፤ ነገር ግን በመጓጓዣ ሐዲዱ ላይ መግባባት እየጠፋ በሀገራችንም ሆነ በዓለማችን በአጠቃላይ ብዙ ጥፋት ተከሥቶአል፤ የሚያስገርመው ነገር ቢኖር ለውይይትና ለመቻቻል ሰፊ ዕድልና ጊዜ አለመስጠቱ ነው፡፡ ጉዳዩ እጅግ ግዙፍ የሆነ የሀገር ህልውና ጉዳይ ስለሆነ በጥልቀት፣ በስፋት፣ በሰከነ አእምሮና አስተሳሰብ በተረጋጋ መንፈስ ሊታይ የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡ አሁን እየተካሄዱ ያሉት የግጭቶች አቅጣጫዎች የሚመስሉ ትንኰሳዎች የኋላ ኋላ ምን ያህል ፀፀት እንደሚያስከትሉ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ድብቅ ምሥጢር አይደሉም፡፡ ሳንግባባ ቀርተን ትናንትና ያጋጩን ነገሮች ብዙ አሳጥተውናል፤ ለማይመለስ ፀፀትም ዳርገውናል፤ አሁንም ተመሳሳይ ስሕተት ፈጽመን ፀፀት ላይ እንዳንወድቅ የፈለገውን ያህል ጊዜ ይውሰድ የፈለገውን ያህል ዋጋ ያስከፍል ያለአንዳች ግጭትና ደም መፍሰስ ሁሉም ነገር ወደዕርቅ፣ ወደሰላምና አንድነት ማምጣት አለብን፤ በነገሩ ላይ ሸማግሌ ከገባበት እግዚአብሔርም ከተጋበዘበት የውይይት ጊዜና ትዕግሥትም ከታከለበት ሁሉም ነገር እየዋለ እያደረ የሰላም ጎሕ እየፈነጠቀ መረጋጋት ሥር እየሰደደ፣ ጥላቻ እየተናደ እንደሚሄድ ጥርጥር የለውም፤ «ዕለት ለዕለት ትጐሥዕ ነቢበ፤ ወሌሊት ለሌሊት ታየድዕ ጥበበ — አንዷ ዕለት ለሌላኛዋ ዕለት መልካም ንግግርን፣ በጎ ሐሳብን ታመነጫለች፤ አንዷ ሌሊትም ለሌላኛዋ ሌሊት የበለጠ ጥበብና ማስተዋልን ትወልዳለች» የሚለው የእግዚአብሔር ቃልም ይህንን ያረጋግጣልና ነው፡፡ በዚህ መንፈስ ጠንክረን ከሠራን ፍሬ እናጣለን ተብሎ አይገመትም፤ ስለሆነም ይህ ዐቢይ ጉባኤ እንደካሁን ቀደሙ ኮሚቴ አቋቁሞ መለያየት ሳይሆን የሀገር ሰላም ጉዳይ በቀጥታ ይመለከተናል በሚል ቅን መንፈስ፣ በተቃርኖ ያሉ ኀይሎችን በግንባር በማግኘትና በማነጋገር የአንድ ሰው ሕይወት እንኳ እንዳይጠፋ ሁሉም የበኩላቸውን እንዲወጡ ጠንክሮ መማፀን አለበት፡፡ የሁሉም ምርጫ ውይይትና ውይይት ብቻ እንዲሆንም በርትቶ በመሥራት ሁሉንም ማሳመን አለበት፤ ከዐቅሙ በላይ ከሆነም ልምዱና ጥበቡ ያላቸው ሀገር ዐቀፍና ዓለም ዐቀፍ ገለልተኛ ወገኖችን በማሳተፍ የዕርቁና የሰላሙ ተልእኮ ግብ እንዲመታ ማድረግ አለበት፤ ይህ ተግባር ወቅቱ ኀላፊነት የጣለበት የቅዱስ ሲኖዶስ ተቀዳሚ ተግባር ነው፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ !
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያናችንን ለከፋ አደጋ የዳረጋት መሠረታዊ ምክንያት የአክራሪዎችና የተቃራኒዎች እንቅስቃሴ መሆኑ በውል ማወቅ አለብን፤ ይሁን እንጂ የእኛ አያያዝም በክፍተት የተሞላ በመሆኑ ከተቃራኒ አካላት ባልተናነሰ ሁኔታ እያስጠቃን ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የሚታዩ ልዩ ልዩ የአሠራር ጒድለቶች ማለትም የአስተዳደር ስልታችን የፋይናንስና የንብረት አያያዛችን ምእመናንን እያበሳጩብን እንደሆነ አንዘንጋ፤ በመሆኑም እነዚህንና ሌሎች ችግሮቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስተካከል ዕውቀቱ፣ ልምዱና ችሎታው ባላቸው ባለሙያዎች በጊዜያዊም ቢሆን መድበን በጥናት ላይ የተመሠረተ መሪ ዕቅድ ዘመናዊ አሠራርን አዘጋጅተው እንዲያቀርቡልን ማድረግ አለብን፡፡ በሠላሳ ዘጠነኛው የሰበካ ጉባኤ ስብሰባ ላይ እንደተጠቀሰው ቤተ ክርስቲያናችን በከባድ ፈተና ላይ መሆኗ ተገልጾአል፤ ስለሆነም ይህ የጥፋት ድርጊት እንዲቆም ሁነኛ መፍትሔ ማስቀመጥ ይኖርብናል፡፡
በመጨረሻም አዲሱ ዓመት ጠንካራ የዕርቅና የሰላም ሥራ ሠርተን ልጆቻችንን ከሥጋትና ከጥፋት የምንታደግበት ይሆን ዘንድ በርትተን እንድንሠራ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሁሉ ልባዊ ጥሪያችንን በእግዚአብሔር ስም እያስተላለፍን፣ ዓመታዊውን የጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ባርከን በጸሎት የከፈትን መሆናችንን እናበሥራለን፤ ጉባኤያችንን ጉባኤ ሐዋርያት፣ ጉባኤ አበው ቅዱሳን ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፤ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32020-10-22 10:02:282025-01-27 10:04:32ጥቅምት 12 ቀን 2013 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. 39ኛው ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to: ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. 39ኛው ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. 39ኛው ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ... Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም የተካሄደው...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top