• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ነሐሴ 1 ቀን 2012 ዓ.ም የ2012 ዓ.ም የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

August 7, 2020

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገር ውስጥና በውጭ የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት፣ እንዲሁም ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!

የይቅርታ ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ!!
“ወሣህሉኒ ለትውልደ ትውልድ ለእለ ይፈርኅዎ
ይቅርታው ለሚፈሩት ለልጅ ልጅ ነው፤”
(ሉቃ. 1፥49)
ይህ ኀይለ ቃል የቅዱስ መጽሐፍ ቀዋሚ ምሰሶ ሆኖ በብዙ ቦታ የሚገኝ ነው፤ ቃሉ እግዚአብሔር ለሚፈሩት የሚያጐናጽፋቸውን የምሕረት ቃል ኪዳን በውስጡ ይዞአል፤ ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንገል ማርያምም እግዚአብሔርን ባመሰገነችበት የምስጋና መዝሙር ይህንን ኀይለ ቃል ተናግራዋለች ፡፡በዚህ ኀይለ ቃል የእግዚአብሔር ይቅርታ ምን ጊዜም የተከበረና እንደተስፋ ቃሉ የሚፈጸም መሆኑ፣ ያም ሊሆን የሚችለው ለሚፈሩት ሰዎች መሆኑ በሚገባ ተገልጾአል ፡፡ የእግዚአብሔር ይቅርታ አጭርና ቀጭን ሳይሆን ለልጅ ልጅ እንደሚሆንም ተብራርቶአል ፡፡
ይህ አባባል እውነት እንደሆነ ለመረዳት ከኛ ከሰዎች የበለጠ ሌላ ምስክር ሊኖር አይችልም፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ሣህሉ ለእግዚአብሔር መልአ ምድረ፣ የእግዚአብሔር ይቅርታ ምድርን መላ” ብሎ እንዳስተማረን ይቅርታው በየጊዜው በዝቶ ባይደረግልን ኖሮ ውሎ ማደሩ የሚቻል አልነበረም፡፡ እግዚአብሔር በነገሩ ሁሉ ኀጢአትን፣ ክፋትን፣ ርኵሰትንና ክሕደትን የሚጠላ አምላክ ነው፤ እኛ ደግሞ ከነኚህ ስሕተቶች ለአንድ ደቂቃ ስንኳ ጸድተን አናውቅም፤ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር በቅጣት ፈንታ ምሕረትንና ይቅርታውን እያበዛልን በምሕረቱ ተጠልለን እንኖራለን፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምን በመውደድ፣ አስተብቍዖቷን፣ ጸሎቷንና ልመናዋን በመሻት ይህንን ጾም ስንጾም በመንፈስ ተሞልታ ያስተማረችንን ፈሪሀ እግዚአብሔር ገንዘብ በማድረግ መሆን አለበት፤ እንደ ተስፋ ቃሉም ለቃሉ በመታዘዝ መሆን አለበት፤ ቃሉ ይቅር እንድትባሉ ይቅርበሉ፣ ሰላምንና አንድነትን አጽንታችሁ ያዙ ይለናልና፡፡
ይህን ይቅርታ ለማግኘት የተጠየቅነው ዋናው ነገር እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ እግዚአብሔርን በእውነት የምንፈራ ከሆነ ይቅርታ ለመስጠትም ሆነ ለመቀበል ዳገት አያግደንምና ነው፤ እግዚአብሔርን መፍራት ማለት በምንሠራው ሥራ፣ በምንናገረው ቃል፣ በምናስበው ሐሳብና ምኞት ሁሉ እግዚአብሔር ያውቅብናል፣ ያየናል፣ ይፈርድብናል፣ የሚል አስተሳሰብ በውስጣችን ኖሮ ክፉ ድርጊትን ከማድረግ እንድንቈጠብ መሆን ማለት ነው ፡፡
ሰው ሁሉ እግዚአብሔርን ከእርሱ ውጪ እንዳለ ሳይሆን በአጠገቡና በመንፈሱ ውስጥ ሆኖ እንደሚያውቅበት ተገንዝቦ እግዚአብሔርን መፍራት አለበት፣ የሰላምና አንድነት መሠረት ከፈሪሀ እግዚአብሔር መነሣት ሲችል ዘላቂና ጠቃሚ ይሆናል፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤
ዘንድሮ የምንጾመው ጾመ ማርያም ሀገራችንና ሕዝባችን በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋ ውስጥ ተከብበው ባሉበት ወቅት ነው፤ የተጋረጡብን ፈተናዎች እግዚአብሔርን ይዘን ካልሆነ በቀር ብቻችን ሆነን የምንወጣቸው አይደሉም፤ በእግዚአብሔር ከለላነት እነዚህን ፈተናዎች ልናልፋቸው ከሆነ እርሱን በመፍራት ከክፋታችን መመለስና ንስሓ መግባት አለብን፤ በነገው ዕለት የምንጀምረው የጾመ ማርያም ሱባዔም ዋና ዐላማው በንስሓ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስና እሱን በመፍራት ለእሱ ተገዢዎች ለመሆን ነው፡፡
ሁሉም እንደሚያውቀው ንስሓ በይቅርታና በዕርቅ መታጀብ ይገባዋል፤ ችግሮቻችን ምን ያህል ቢበዙም ለእግዚአብሔር ብለን በምንፈጽመው ይቅርታና ዕርቅ፣ በምናረጋግጠው ሰላምና አንድነት ተሸናፊዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ችግሮችን ለማሸነፍ ብሎም ለማስወገድ ከይቅርታና ዕርቅ፣ ከሰላምና አንድነት የተሻለ አማራጭ እንደሌለ ልሂቃኖቻችንም ሆኑ ሕዝቦቻችን በውል መገንዘብ አለባቸው ፡፡
ኢትዮጵያ የምትባለው ሀገር የዚህ ትውልድ ሀገር ብቻ አይደለችም፤ ያለፉ አባቶች፣ የሚመጡ ትውልዶችም የኢትዮጵያ ባለቤቶች ናቸው ፡፡ እኛ በክብ ጠረጴዛ ተገናኝተን ተወቃቅሠንና ተመካክረን ችግራችንን በተሸንፎ ማሸነፍ ጥበብ ማረም ካቃተን ቢያንስ ኢትዮጵያን ባለችበት ሁናቴ ለባለ መብቱ መጪው ትውልድ የማስተላለፍ ግዴታ እንዳለብን መዘንጋት የለብንም፤ ነገሮችን ሁሉ በትዕግሥት፣ በአርቆ አስተዋይነትና በሰላማዊ ሁኔታ ለማስተናገድ ያላሰለሰ ጥረት ማድረግ ይገባናል፤ በመሆኑም ኢትዮጵያ የገጠሟትን ፈተናዎች ሁሉ ተቋቍማ በአሸናፊነት መሻገር የምትችለው እግዚአብሔርን በመፍራት ለይቅርታና ለዕርቅ ስንዘጋጅ ነው፤ ስለዚህ ይህ ግንዛቤ ተወስዶ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ቆመናል የሚሉ የፖለቲካ ተፎካካሪ ወገኖች ሁሉ አንድ ላይ ተገናኝተውና በክብ ጠረጴዛ ሆነው በመወያየት የሀገሪቱን አንድነት፣ ሰላምና ልማት እንዲያስቀጥሉ በዚህ አጋጣሚ በእግዚአብሔር ስም እንማፀናለን ፡፡
በመጨረሻም፤ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ የጾም ሱባዔ በኮረና ቫይረስ እንዳይጎዳ ጥንቃቄ በማድረግ የሱባኤውን ወቅት ስለሀገር ሰላምና አንድነት በኀዘን፣ በምሕላ፣ በጸሎት፣ በንስሓና በፍቅር፣ የተቸገሩትንም በመርዳት እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲያሳልፍ አባታዊና መንፈሳዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ይቀድስ፤ አሜን!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32020-08-07 14:04:212025-01-28 14:05:16ነሐሴ 1 ቀን 2012 ዓ.ም የ2012 ዓ.ም የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ከግንቦት 05 ቀን እስከ ግንቦት 06 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከግንቦት 05 ቀን እስከ ግንቦት 06 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከግንቦት 05 ቀን እስከ ግንቦት 06 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው... Link to: መስከረም 1 ቀን 2013 ዓ.ም. የርእሰ ዐውደ ዓመት ቃለ ቡራኬ Link to: መስከረም 1 ቀን 2013 ዓ.ም. የርእሰ ዐውደ ዓመት ቃለ ቡራኬ መስከረም 1 ቀን 2013 ዓ.ም. የርእሰ ዐውደ ዓመት ቃለ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top